ሀዲያ ሆሳዕና በሜዳው ማድረግ የነበረበትን ጨዋታ በቅጣት ምክንያት በገለልተኛ ሜዳ እንዲጫወት በዲሲፒሊን ኮሚቴ ተወስኖበታል፡፡ ቅጣቱን ተከትሎ በ23ኛው ሳምንት ሃዲያ ሆሳዕና በሜዳው ከአዳማ ጋር መጫወት የሚገባውን ጨዋታ በሀዋሳ ከተማ የሚያካሂድ ይሆናል፡፡
ለቅጣቱ ምክንያት የሆነው ሀዲያ ሆሳዕና ከ ቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር ከተደረገው ጨዋታ መጠናቀቅ በኋላ የክለቡ ደጋፊዎች በክለቡ አመራር ላይ ባነሱት ተቃውሞ በተፈጠረው ግርግር ነው፡፡
በዕለቱ የተከሰተው ግርግር በቶሎ ባለመብረዱ ምክንያት የፀጥታ ሃይሎች ግርግሩን ለማብረድ የአስለቃሽ ጋዝ እስከመጠቀም ደርሰው እንደነበር የሚታወስ ነው፡፡
ሀዲያ ሆሳዕና በ21ኛው ሳምንት በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መሸነፉን ተከትሎ 5 ጨዋታ እየቀረው ከኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ መውረዱን ማረጋገጡ ይታወቃል፡፡