የኢትዮጵያ ከ17 አመት በታች ፕሪሚየር ሊግ የማጠቃለያ ውድድር ዛሬ በአዳማ አበበ ቢቂላ ስታድየም ፍጻሜውን አግኝቷል፡፡ ሀዋሳ ከተማም ውድድሩን በቻምፒዮንነት አጠናቋል፡፡
07:00 ላይ ከፍፃሜው በፊት በተካሄደው የደረጃ ጨዋታ አዳማ ከተማ መከላከያን 3-1 በማሸነፍ 3ኛ ደረጃ ይዞ አጠናቋል፡፡
የአዳማ ከተማን የድል ግቦች ኢሳ ንጉሴ (2) እና የኋላሸት ፍቃዱ ሲያስቆጥሩ የመከላከያን አቤል ነጋሽ አስቆጥሯል፡፡
ኢሳ ንጉሴ ዛሬ ያስቆጠራቸውን ጨምሮ የግብ መጠኑን 5 በማድረስ ከመከላከያው ዮሃንስ ደረጄ ጋር በጋራ ከፍተኛ ግብ አስቆጣሪ ሆኖ አጠናቋል፡፡
09:00 ላይ በተካሄደው የፍጻሜ ጨዋታ ሀዋሳ ከተማ ሲዳማ ቡናን 3-1 አሸንፎ የውድድሩ ቻምፒዮን ሆኗል፡፡
ወንድማገኝ ታደሰ (2) እና እስራኤል እሸቱ የሀዋሳ ከማን ግቦች ሲያስቆጥሩ አቤኔዘር አስፋው የሲዳማ ቡናን ብቸኛ ግብ አስቆጥሯል፡፡
ከጨዋታው መጠናቀቅ በኋላ የሽልማት ስነስርአት የተከናወነ ሲሆን የፌዴሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ጁነይዲ ባሻ እና የውድድር እና ስነሰርአት ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ አሊሚራ መሃመድ ሽለልማቶቹን አስረክበዋል፡፡
ኮከብ ተጫዋች
የመከላከያው ዮሃንስ ደረጄ በውድድሩ ባሳየው ድንቅ አቋም ኮከብ ተጫዋች ተብሎ 5 ሺህ ብር ተሸላሚ ሆኗል፡፡ ዮሃንስ በኮከብ ግብ አግቢነት በማጠናቀቅም የውድድሩ ክስተት ሆኗል፡፡
ኮከብ ግብ አግቢዎች
በማጠቃለያ ውድድሩ 5 ግቦች ያስቆጠሩት የመከላከያው ዮሃንስ ደረጄ እና የአዳማ ከተማው ኢሳ ንጉሴ በከፍተኛ ግብ አግቢነት እያንዳንዳቸው የ5ሺህ ብር ተሸላሚ ሆነዋል፡፡
በዞናቸው ውድድር ከፍተኛ ግብ ላስቆጠሩ ተጫዋቾችም ሽልማት የተበረከተ ሲሆን ከደቡብ-ምስራቅ ዞን የኋላሸት ፍቃዱ (ሀዋሳ) እና ወንድማገኝ ታደሰ (አዳማ) በ4 ግቦች ፣ ከመካከለኛ ዞን የሐረር ሲቲው ታድዮስ አዱኛ በ16 ግቦች በኮከብ ግቅ አግቢነት እያንዳንዳቸው የ3 ሺህ ብር ተሸላሚ ሆነዋል፡፡
ምስጉን ዳኞች
ዋና ዳኛ አለማየሁ ለገሰ የ5ሺህ ፣ ረዳት ዳኛ ካህሳይ ጥኡመ የ3ሺህ ብር ሽልማተት ተበርክቶላቸዋል፡፡
ኮከብ ግብ ጠባቂ
የሀዋሳ ከተማው አላዛር መርሄ የውድድሩ ኮከብ ግብ ጠባቂ ተብሎ 3ሺህ ብር ተሸልሟል፡፡
ኮከብ አሰልጣኝ
የሀዋሳ ከተማ አሰልጣኝ ተመስገን ዳና የውድድሩ ኮከብ አሰልጣኝ ተብለው የ10ሺህ ብር ሽለልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡
የስፖርታዊ ጨዋነት ዋንጫ
መከላከያ የስፖርታዊ ጨዋነት ዋንጫን የግሉ አድርጓል፡፡ መከላከያ ዘንድሮ የተካሄዱን የወንዶች ፕሪሚየር ሊግ ፣ የሴቶች ፕሪሚየር ሊግ እና የ17 አመት በታች ፕሪሚየር ሊግ የስፖርታዊ ጨዋነት ዋንጫዎች ማንሳት ችሏል፡፡
የዋንጫ እና ሜዳልያ ሽልማቶች
ደደቢት እና ሀዋሳ ከተማ የየዞናቸውን ውድድሮች በቻምፒዮንነት በማጠናቀቃቸው ዋንጫ ሲበረከትላቸው 3ኛ ደረጃ ላገኘው አዳማ ከተማ የነሀስ ሜዳልያ እና 20ሺህ ብር ፣ 2ኛ ደረጃ ይዞ ላጠናቀቀው ሲዳማ ቡና የብር ሜዳልያ እና 30ሺህ ብር ፣ ለቻምፒዮኑ ሀዋሳ ከተማ የዋንጫ ፣ ወርቅ ሜዳልያ እና 50ሺህ ብር ተሸላሚ ሆነዋል፡፡