የአፍሪካ እግርኳስ ኮንፌድሬሽን በየዓመቱ የሚያካሄደው የአፍሪካ የአመቱ ምርጥ ተጫዋች ምርጫ ዕጩዎች ከ30 ወደ 5 ቀንሰዋል፡፡ በናይጄሪያ አቡጃ በሚካሄደው የሽልማት ስነ-ስርዓት በአፍሪካ የሚጫወት የአፍሪካ ምርጥ ተጫዋች፣ የዓመቱ የአፍሪካ ምርጥ ተጫዋች፣ የዓመቱ የአፍሪካ ምርጥ ሴት ተጫዋች፣ የዓመቱ ምርጥ የአፍሪካ ክለብ፣ የዓመቱ ምርጥ ብሄራዊ ቡድን፣ የአመቱ ተስፋ የተጣለበት ተጫዋች እና ወጣት ተጫዋች ምርጫ ይደረጋል፡፡
በአመቱ አፍሪካ ምርጥ ተጫዋች ዝርዝር ውስጥ በአፍሪካ ሊጎች ውስጥ የሚጫወት አንድም ተጫዋች የለም፡፡ አምስቱም ተጫዋቾች በአውሮፓ ሊጎች የእግርኳስ ህይወታቸውን እየመሩ ይገኛሉ፡፡ የጋባኑ ፒየር ኤምሪክ ኦባሚያንግ ለሁለተኛ ተከታታይ ግዜ የመመረጥን አምስቱ ውስጥ መግባት ችሏል፡፡ አጥቂው የ2015 የአፍሪካ የአመቱ ምርጥ ተጫዋች ተብሎ ተመርጧል፡፡ ከቢቢሲ የአመቱ የአፍሪካ ምርጥ ተጫዋች ዕቹዎች ውስጥ በአስገራሚ መልኩ መግባ ያልቻለው መሃመድ ሳላ ካፍ በሚያዘጋጀው ሽልማት ዝርዝር ውስጥ ገብቷል፡፡ በእንግሊዝ የሚገኙት ሰይዶ ማኔ፣ ሪያድ ማህሬዝ እና ኢስላም ስሊማኒ በዕቹዎቹ ውስጥ የተካተቱ ሌሎች ተጫዋቾች ናቸው፡፡ ዕጩዎቹ የሚከተሉት ናቸው፡፡
- ፒየር ኤምሪክ ኦቦሚያንግ (ጋቦን እና ቦሪሲያ ዶርትሙንድ)
- ሪያድ ማህሬዝ (አልጄሪያ እና ሌስተር ሲቲ)
- ሰይዶ ማኔ (ሴኔጋል እና ሊቨርፑል)
- መሃመድ ሳላ (ግብፅ እና ሮማ)
- ኢስላም ስሊማኒ (አልጄሪያ እና ሌስተር ሲቲ)
በአፍሪካ የሚጫወት የአመቱ ምርጥ ተጫዋች ዝርዝር በካፍ ቻምፒየንስ ሊግ አሸናፊው ማሜሎዲ ሰንዳውንስ ተጫዋቾች ተጠለቅልቋል፡፡ የሰንዳውንሶቹ ካማ ቢሊያት፣ ኪገን ዶሊ፣ ሆሎምፖ ኬኬና እንዲሁም ግብ ጠባቂው ዴኒስ ኦኒያንጎ የአምስቱ ዕጩዎቹ ውስጥ ገብተዋል፡፡ ኬኬና ከዚህ ምርጫ ባሻገር በአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ ካሜሮን ላይ ከራሱ ግብ ክልል ያስቆጠረው ግብ ለፊፋ ፑሽካሽ ሽልማት ዕጩዎች ውስጥ እንደሚያስገባው ይጠበቃል፡፡ ቲፒ ማዜምቤ የካፍ ኮንፌድሬሽን ካፕ አሸናፊ እንዲሆን ቁልፍ ሚናን የተጫወተው ሬንፎርድ ካላባ እጩዎቹ ውስጥ የገባ ሌላኛው ተጫዋች ነው፡፡ ዕጩዎቹ የሚከተሉት ናቸው፡፡
- ካማ ቢሊያት (ዚምባቡዌ እና ማሜሎዲ ሰንዳውንስ)
- ኪገን ዶሊ (ደቡብ አፍሪካ እና ማሜሎዲ ሰንዳውንስ)
- ሬንፎርድ ካላባ (ዛምቢያ እና ቲፒ ማዜምቤ)
- ሆሎምፖ ኬኬና (ደቡብ አፍሪካ እና ማሜሎዲ ሰንዳውንስ)
- ዴኒስ ኦኒያንጎ (ዩጋንዳ እና ማሜሎዲ ሰንዳውንስ)
አምስቱን ዕቹዎች የመመረጡ ሂደት ላይ የተሳተፉት የካፍ ሚዲያ ኮሚቴ አባላት፣ የካፍ ቴክኒካል እና ልማት ኮሚቴ አባላት እና ግማሽ የሚሆኑት የኤክስፐርቶች ፓናል አባላት ናቸው፡፡ አሸናፊውን ለመለየት በሚካሄዱ የመጨረሻ ምርጫ ውስጥ የሚሳተፉት 54ቱ የካፍ አባል ሃገራት አና ተባባሪ አባላት የሆኑት የሪዩኒየን ደሴት እና ዛንዚባር እንዲሁም ግማሽ የሚሄኑት የአክስፐርቶች ፓናል አባላት ይሆናሉ፡፡ የኤክስፐርቶች ፓናል አባላት 20 ናቸው፡፡ የ2016ቱ ሽልማት በፈረንጆቹ ጥር 5 2017 አቡጃ ላይ ይካሄዳል፡፡ ሽልማቱን ስፖንሰር ያደረገው የቴሌኮሚኒኬሽን ድርጅት የሆነው ግሎባኮም ነው፡፡