በሚልኪያስ አበራ
በሰኞ ምሽቱ የአዲስ አበባ ስታድየም የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ጨዋታ ኢትዮጵያ ቡና ዳሽን ቢራን አሰተናግዶ 0-0 በሆነ አቻ ውጤት ተለያይቷል፡፡
በአሰልጣኝ ሳምሶን አየለ የሚመራው እንግዳው ቡድን በሁለት ጠንካራና ወደኋላ አፈግፍገው በሚጫወቱ ተከላካይ አማካዮች የተዋቀረውን 4-4-2 (4-4-1-1) የተጫዋቾች የሜዳ ላይ አደራደርን የተገበረ ሲሆን የጥላሁን መንገሻ ኢትዮጵያ ቡና ደግሞ ሁለቱን መስመር አጥቂዎች መጠቀም የሚያስችለውን 4-4-2 ፎርሜሽን ተጠቅሟል፡፡
(ምስል 1)
የመጀመርያ 45
በዚህኛው የጨዋታ ክፍለ ጊዜ ኢትዮጵያ ቡናዎች ወደ መሃል ሜዳው ተጠግተው በሚከላከለው የተከላካይ መስመራቸው አማካኝነት በሜዳው ቁመት በተጫዋች አደራደር መካከል የሚፈጠረውን ክፍተት ለማጥበብ ችለዋል፡፡ በማጥቃት አጨዋወት ሒደት (attacking phase) ተቀራርበው አጫጭር ቅብብሎችን በተጋጣሚ ሜዳ ማድረግ ቢችሉም እጅግ የተደራጀውንና በከፍተኛ ጥንቃቄ የሚከላከለውን የዳሽን የተከላካይ መስመር አልፈው መሄድ አልቻሉም፡፡ high-line defence ሰርተው መጨወታቸው በተጋጣሚያቸው ሜዳ ላይ መጠነኛ የኳስ ቁጥጥር የበላይነት አስገኝቷል፡፡
አልፎ አልፎ አስቻለውና ጥላሁን ወደ ዳሽን የግብ ክልል ገብተው ሲመለሱ መጠነኛ መዘግየት (delay) ይታይባቸው ነበር፡፡ አህመድ እና ዴቪድ ከአማካዮች ጀርባ በመጀኘት ለመስመሩ ከለላ(ሽፋን) ከመስጠታቸው ባሻገር በቡድኑ የማጥቃ ሽግግር (attacking transition) ላይ የነበራቸው ሚና መልካም ነበር፡፡ በቀኝ መስመር ዴቪድ በሻህ አንዳንዴ ቶሎ ተመልሶ ቦታውን የመሸፈን እና በመሃል ተከላካዮች እና በእሱ መካከል ያለውን ክፍተት (channel) ሲያጠብ የመማይታይባቸው አጋጣሚዎች ተከስተዋል፡፡ ይህም የዳሽኖቹ አምሳሉ ፣ የተሻ እና መድሃኔ በግራ መስመራቸው ተደጋጋሚ የሶስትዮሽ ግንኙነት በማድረግ (ትሪያንግል ለመስራት) የመቀባበያ አማራጮችን በመፍጠር መስመሩን የማጥቃት መንገዳቸውን (attacking phase) ለማድግ ሲጥሩ ታይተዋል፡፡
የአማራው ክልል ተወካይ ቡድን በሁለቱ ተንቀሳቃሽ የተከላካይ አማካዮች የታታዘ (በአስራት እና ሳሙኤል) ጠንካራ የመሃል ቅርፅ አሳይቷል፡፡ የመልሶ ማጥቃት አጨዋወትን ለመተግበር ያለመ በሚመስለው አቀራረባቸው ቶሎ ቶሎ የሚቀያየር የጨዋታ ሒደቶች መጠነኛ የማጥቃት ሁኔታዎች ለመፍጠር ሞክረዋል፡፡ አልፎ አልፎ በረጅሙ የሚሉት ኳሶች ለታለመላቸው ተጫዋቾች መድረስ ባይችሉም ከመከላከል ወደ ማጥቃት የሚያደርጉት ሽግግግር ግን ፈጣን ነበር፡፡
መድሃኔ ታደሰ በሁለገብነት ሚና ወደ ኋላ እጅግ ያፈገፈገውን የአማካይ ክፍል እና የአጥቂውን መስመር ለማገናኘት ( link ሲያደርግ) እንዲሁም በቡድኑ የመከላከል አጨዋወት (defending phase) የነበረው ድርሻ የጎላ ነበር፡፡
(ምስል 2)
ሁለተኛው አጋማሽ
ሁለቱም ቡድኖች የተጫዋች ቅያሪ ያካሄዱት በሁለተኛው 45 በመጀመርያዎቹ 15 ደቂቃዎች ውስጥ ነበር፡፡ በዳሽን ቢራ በኩል የነበረው አጥቂ ተጫዋችን በሌላ ቦታ ተሰላፊ መቀየር ሲሆን የቡናዎች ለውጥ ደግሞ በቡድኑ የመጀመርያ አጋማሽ የነበረውን የተጫዋቾች ሚና መጠነኛ ቅያሪ ያሳየ ነበር፡፡
ኢትዮጵያ ቡናዎች በጨዋታው ብዙም የማጥቃት እንቅስቃሴ (attacking phase) ላይ ብዙም አመርቂ ውጤት ያላሳየውን ዴቪድ በሻሀ ሮቤል ግርማን አስገቡ፡፡ ይህም በግራ መስመር ላይ የነበረው አህመድ ወደ ቀኝ መስመር አሸጋገረው፡፡ጥላሁን ወጥቶ ዳዊት ሲገባም የposition ለውጥ ተደርጎ ነበር፡፡መስኡድ የጥላሁንን ፤ ዳዊት ደግሞ የመስኡድን ቦታ ተረክበዋል፡፡
ነገር ግን ይህ ለውጥ ለቡናዎች አነስተኛ የማጥቃት ጫና መፍጠር ቢያስችላቸውም አሉታዊ ገፅታም ነበረው፡፡ መስኡድ እና በተደጋጋሚ ከመስመር ወደ መሃለኛው የሜዳ ክፍል ሲገቡ (cut inside) የመስመር ተከላካዮች ይበልጥ ለተጋጣሚ የመስመር አማካዮች ተጋላጭ ሲሆኑ ታይቷል፡፡ ዳሽኖች እጅግ በመከላከሉ ላይ በማተኮራቸው እንጂ ይህንን ክፍተት መጠቀም ይችሉ ነበር፡፡
ጥሩ ሲንቀሳቀሱ የነበሩት የቡና የመሃል ተከላካዮች (ኤፍሬም እና ሚልዮን) እስከ ተጋጣሚ ሜዳ ክልል ድረስ እየመጡ ኳሷን ሲነጥቁ ተመልክተናል፡፡ ቡድኑ (ቡና) የተጠና ኳስን የመቀባበል ስርአትን አላሳየም፡፡ ይህም የቡድኑን ጨዋታ ፍጥነት (tempo) የመቆጣጠር ፣ ተከላካይ ሰንጣቂ የሃል ኳሶችን (through ball) ለአጥቂዎች ማድረስ እንዲሁም ቡድንን በማጥቃት አጨዋወት የመምራት ፣ የማደራጀት እና ውህደት (coherence) የመፍጠር ችግር ተስተውሎበታል፡፡ በዳሽን ሜዳ (attacking third) አካባቢ በዝተው ( overload አድርገው) ቢጫወቱም የተጠቀጠቀውን የዳሽን የመከላከል መስመር ማለፍ የሚያስችል ስልት እና እድል መፍጠር አልቻሉም፡፡ ተጋጣሚው ቡድን ዳሽን ደግሞ የመከላከልን ብቻ አማራጭ ባደረገ መንገድ መቅረቡ ቡናዎች ሲፈጥሩ የነበሩትን ክፍተቶች አንዳይጠቀም ምክንያት ሆኗል፡፡ ጫናን እየተቋቋሙ በመልሶ ማጥቃት ለመጫወት የሚያደርጉት ጥረት በላይኛው ሜዳ የሚጣሉ ረጃጅም ኳሶች ላይ የተመሰረተ ቢሆንም እነዚህን ቅብብሎች በትክክለኛው ቦታ ለትክክለኛው ተጫዋች ለማድረስ የተመጠኑ እና ልኬታቸውን የጠበቁ አልነበሩም፡፡
የዳሽን የመስመር አማካዮች (የተሻ እና ኤርሚያስ) የመቀባበያ አማራጮችን እና የማጥቃት ማእዘናትን ከማስፋት ይልቅ ወደ ኋላ አፈግፍገው የመከላከል ሃላፊነትን ሲተገብሩ ተስተውሏል፡፡ በእርግጥ የቡድኑ የመከላከል ቅርፅ እጅግ የተደራጀ (organized) ቢሆንም የቦታው ተጫዋቾች ልምድ አይነተኛ አስተዋፅኦ አበርክቷል፡፡ እቅዳቸውን ተግባራዊ ማድረጋቸው (አንድ ነጥብ ማግኘት መቻላቸው) ቢታይም ማጥቃት ላይም መጠነኛ መሻሻል ቢያሳዩ መልካም ነው፡፡
(ምስል 3)