በወንጂ ስኳር ፋብሪካ ስታዲየም በመካሄድ ላይ ባለው በኢትዮጵያ ሴቶች ፕሪምየር ሊግ የማጠቃልያ ውድድር ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ዳሽን ቢራ ለፍፃሜ መድረሳቸውን አረጋግጠዋል፡፡ በፍፃሜ ግማሽ ሲዳማ ቡናን የገጠመው ንግድ ባንክ በማሸነፉ አሁንም የፍፃሜ ተፋላሚ ሆኗል፡፡ ሁለቱ ቡድኖች መደበኛውን የጨዋታ ክፍለ ጊዜ 1ለ1 በሆነ የአቻ ውጤት ጨርሰዋል፡፡ አሸናፊውን ለመለየት በተሰጠው የመለያ ምት ንግድ ባንክ 4ለ3 ማሸነፍ ችሏል፡፡
አምና ሊጉን በሁለተኛነት የጨረሰው ደደቢት በዳሽን ቢራ ተሸንፎ ለፍፃሜ ማለፍ ሳይችል ቀርቷል፡፡ ደደቢት እና ዳሽን መደበኛውን የጨዋታ ጊዜ 2ለ2 ጨርሰዋል፡፡ ዳሽን በመለያ ምት 5ለ3 በማሸነፍ ለፍፃሜ መድረስ ችሏል፡፡
ንግድ ባንክ እና ዳሽን በኢትዮጵያ የሴቶች ፕሪምየር ሊግ ፍፃሜ ይገናኛሉ፡፡ የፍፃሜ ጨዋታው ቅዳሜ ይካሄዳል፡፡ ለደረጃ ደደቢት እና ሲዳማ ቡና ዛሬ ይጫወታሉ፡፡ የዓምናው የሊጉ አሸናፊ ንግድ ባንክ አሁንም አሸናፊ እንደሚሆን ቅድመ ግምት አግኝቷል፡፡