ጅማ አባጅፋር ያስፈረማቸው የውጭ ተጫዋቾችን በነገው ጨዋታአይጠቀምም

ከሜዳ ውጭ በሚፈጠሩ የተለያዩ ጉዳዮች በተደጋጋሚ ሲቸገር የሚስተዋለው ጅማ አባጅፋር አዲስ ያስፈረማቸው የውጭ ተጫዋቾችን በነገው ጨዋታ አይጠቀምም።

ጅማ አባጅፋር ለ2012 የውድድር ዘመን ወደ ቡድኑ ከቀላቀላቸው ተጫዋቾች መካከል ጋናዊው የግብጠባቂው መሐመድ ሙንታሪ፣ ተከላካዩ አሌክስ አሙዙ እና አጥቂው ያኩቡ መሐመድ ይገኙበታል። በአደየዳማ ከተማ ዋንጫ ላይ ባሳዩት መልካም እንቅስቃሴ በቀጣይ አባጅፋሮች የሊጉ በሚኖራቸው ጨዋታ ላይ ጥሩ አገልግሎት ይሰጣሉ ተብሎ ሲጠበቅ አስቀድሞ ማለቅ የሚገባው ፓስፖርት ጉዳይ ማለቅ ባለመቻሉ ምክንያት ከነገው ጨዋታ ውጭ መሆናቸው ተረጋግጧል።

ከፍተኛ ብር እየወጣ በክለቡ የአስተዳደር ክፍል ችግር ምክንያት በነገው ጨዋታ ላይ እነዚህን ተጫዋቾች አለማግኘት አሰልጣኝ ጳውሎስ ጌታቸው የቡድን ስብስብ ላይ አሉታዊ ተፅእኖ ያደርጋል ተብሎ ተሰግቷል።

ሰበታ ከተማም በተመሳሳይ ችግር አስቀድሞ መጠናቀቅ የሚገባው የውጭ ተጫዋቾቹ የፓስፖርት ጉዳይ ባለመጠናቀቁ በአአ ከተማ ዋንጫ ሰበታ ሁለተኛ ደረጃ ይዞ እንዲያጠናቅቅ ከፍተኛ አስተዋፆኦ ያበረከቱት ግብጠባቂው ዳንኤል አጃይ፣ ተከላካዮ ሳቪዮ ካቩጎ፣ አጥቂው ባኑ ዲያዋራን በዛሬው እለት በወልዋሎ 3-1 በተሸነፈበት ጨዋታ ላይ ሳይሰለፉ መቅረታቸው ታይቷል።


© ሶከር ኢትዮጵያ