የአሰልጣኞች አስተያየት | ስሑል ሽረ 1-1 ጅማ አባ ጅፋር

በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ አስረኛ ሳምንት መቐለ ላይ ጅማ አባ ጅፋር ከ ስሑል ሽረ 1-1 በሆነ አቻ ውጤት ካጠናቀቁት ጨዋታ በኋላ የሁለቱ ቡድኖች አሰልጣኞች አስተያየታቸውን ሰጥተዋል።

👉 “ያለአግባብ የምናባክናቸው የጎል ዕድሎች ዋጋ እያስከፈሉን ነው” ሳምሶን አየለ (ስሑል ሽረ)

ስለ ጨዋታው

ያለአግባብ የምናባክናቸው የጎል ዕድሎች ዋጋ እያስከፈሉን ነው። ምንም እንኳ እያሸነፍን ብንመጣም ባለፉት ጨዋታዎች ያየናቸው ስህተቶች ዛሬም ዋጋ አስከፍለውናል። ተጋጣሚያችን ከሽንፈት ስለመጣ ቢያንስ አንድ ነጥብ ይዞ ለመውጣት ያስባል ብለን በመገመት ኳሱን ይዘን የግብ ዕድል ለመፍጠር ነበር የገባነው። ከዛ ባለፈ በመሀል ተካላካዮቻችን መዘናጋት ነበር። እዛ ላይ ጠንክረን እንሰራለን።

ስለ ሁለተኛው አጋማሽ አቀራረብ

ኳሱን ተቆጣጣሮ ለመጫወት አስበን ነው የገባነው። እነሱ በመልሶ ማጥቃት ከማጥቃት ውጪ አብዛኛውን ጊዜ ኳሱ ከኛ ጋር ነበር። እንደ አጠቃላይ ጨዋታው ጥሩ ነበር። ሦስት ነጥብ ለማግኘት አስበን ገብተን አንድ ነጥብ ይዘን ወጥተናል።

👉 “መሐል ሜዳ ላይ ብልጫ ነበረን” ጳውሎስ ጌታቸው (ጅማ አባ ጅፋር)

ስለ ጨዋታው

ኳሱን ይዘን ነው የተጫወትነው። በተለይም የመጀመርያው አጋማሽ ብልጫ ነበረን። የማይሆን ኳስ ነው የተቆጠረብን። ስለ ዳኝነት ስህተት አላወራም። በእጅ የተቆጠረ ኳስ ነው፤ ግን ለዳኛው ትቼዋለው። በሜዳችን ተሸንፈን ስለመጣን አጥቅተን አሸንፈን ለመውጣት ነው። ሜዳው ለኛ አጨዋወት የተመቸ ነው። በዚህም በጣም ደስተኛ ነኝ። ሜዳው አስተማማኝ ነው።

መሀል ሜዳ ላይ ብልጫ ነበረን። ረጃጅም ኳሶች እንደሚጠቀሙ አስበነው ነው የመጣነው። በአጠቃላይ ጨዋታው ሚዛናዊ ነበር።

ስለ አጥቂ ችግራቸው

ከዕረፍት በፊት አራት ያለቀላቸው ኳሶች ነው ያመከነው። ከአራቱ ነው አንዱ ያገባነው። ተፈጥሯዊ አጥቂ በዚህ ጊዜ እየቀረ ነው። ተጫዋቾቼ በሙሉ ጎል አስቆጣሪ ሊሆኑ ይገባል።


© ሶከር ኢትዮጵያ