የአሰልጣኞች አስተያየት | አዳማ ከተማ 3-0 ኢትዮጵያ ቡና 

በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ 11ኛ ሳምንት አዳማ ከተማ በሜዳውና በደጋፊው ፊት ኢትዮጵያ ቡናን 3-0 በሆነ ውጤት ካሸነፈበት ጨዋታ መጠናቀቅ በኃላ የአዳማ ከተማው ም/አሰልጣኝ አስቻለው ኃይለሚካኤል ተከታዩን ሀሳብ ሰጥተዋል።


👉 “አስተዳደሩ አፋጣኝ ምላሽ የሚሰጥ ከሆነ በተሻለ ወደ መስመር ተመልሰን ጥሩ ነገር መስራት እንችላለን”- አስቻለው ኃይለሚካኤል (አዳማ ከተማ)

ስለጨዋታው

“በሁለቱም ቡድኖች በኩል ጥሩ የኳስ ፍሰት የታየበት ጨዋታ ነበር። በዛሬው ጨዋታ ትልቁ ነገር እንደከዚህ ቀደም እንደተሸነፍንባቸው ጨዋታዎች ኳስን ተቆጣጥረን ተጫውተን የነበረብን የግብ እድሎችን የመቀየር ችግር በደንብ ዛሬ ቀርፈን ከጥሩ ጨዋታ ጋር ማሸነፍ ችለናል።”

ከሜዳ ውጭ ነጥብ ስለጣሉበት ሒደት

“በዚህ ጉዳይ ላይ አስምሬ መናገር የምፈልገው በተለይ ወደ ክልል ሜዳዎች ሲወጣ ዳኞች ላይ ጫና አለ፤ እዚህ እኛ ጋርና አዲስ አበባ ስታዲየም ላይ ብቻ ዳኛ ላይ ጫና የሚያሳድር የለም። ከዚህ ውጭ የተወሰኑ ሜዳዎች ላይ ዳኞች ላይ ከፍተኛ ጫና ከመኖሩ የተነሳ የሚወሰኑ ውሳኔዎች ለመቀበል እጅግ አስቸጋሪ ናቸው።”

ይህን ውጤት ለማስቀጠል

“ይህ የሚወሰነው በዋነኝነት በአስተዳደሩ የሚወሰን ነው። አስተዳደሩ አፋጣኝ ምላሽ የሚሰጥ ከሆነ በተሻለ ወደ መስመር ተመልሰን ጥሩ ነገር መስራት እንችላለን። እንደምታዩት አሁን ላይ ችግር ላይ ነን ይፈታል ቢባልም ያየነው ነገር የለም ፤ አስተዳደሩ ይህን ጉዳይ በጊዜ ቢፈታልን ትልቅ ውጤት ይዘን እንወጣለን ብዬ አስባለሁ።”

*የኢትዮጵያ ቡና አሰልጣኝን ሀሳብ ለማካተት ያደረግነው ጥረት ከጨዋታው መጠናቀቅ በኃላ የተወሰኑ የኢትዮጵያ ቡና ደጋፊዎች የቡድኑ አባላት ላይ ባሰሙት ከፍተኛ ተቃውሞ ምክንያት መስጠት ባለመቻላቸው ማካተት ሳንችል ቀርተናል።

© ሶከር ኢትዮጵያ