አዳማ ከተማ ወሳኝ ዝውውር አጠናቋል

በትናንትናው ዕለት ዘርዓይ ሙሉን በአሠልጣኝነት የሾሙት አዳማ ከተማዎች የአጥቂ አማካይ ማስፈረማቸው ተረጋግጧል።

ከቀናት በፊት ከአሠልጣኝ አስቻለው ጋር የተለያዩት አዳማ ከተማዎች በትላንትናው ዕለት የቀድሞውን የሲዳማ ቡና አሠልጣኝ ዘርዓይ ሙሉን መሾማቸው ይታወቃል። በወራጅ ቀጠናው ላይ የሚገኘው አዳማ ከተማም በሁለተኛው ዙር የቤትኪንግ ፕሪምየር ሊግ ካለበት አስጊ ቀጠና ለመውጣት ራሱን አጠናክሮ ለመቅረብ እንቅስቃሴ ጀምሯል። በዚህም የአጥቂ አማካዩን ኤልያስ ማሞን ወደ ስብስቡ መቀላቀሉ ታውቋል።

የቀድሞ የቅዱስ ጊዮርጊስ፣ ኢትዮጵያ ቡና፣ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ እና ድሬዳዋ ከተማ ተጫዋች የነበረው ኤልያስ ከሳምንታት በፊት ከቡርትካናማዎቹ ጋር ከተለያየ በኋላ በዛሬው ዕለትም የፈጠራ ችግር የሚስተዋልበትን አዳማ ከተማን መቀላቀሉ ታውቋል።


© ሶከር ኢትዮጵያ