ቡና እና ሀዋሳ በ20 ዓመት በታች ፕሪምየር ሊግ የየምድባቸው አሸናፊነታቸውን አረጋግጠዋል

በኢትዮጵያ ከ20 ዓመት በታች ፕሪምየር ሊግ 13ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ዛሬ ተከናውነው ኢትዮጵያ ቡና እና ሀዋሳ ከተማ የየምድባቸው አሸናፊ መሆናቸውን ያረጋገጡበት ውጤቶች ተመዝግበዋል።

በምድብ ሀ መከላከያ ሜዳ 05:00 ላይ በመከላከያ እና በኢትዮዽያ ቡና መካከል የተደረገው ጨዋታ በኢትዮዽያ ቡና 3 – 2 አሸናፊነት ተጠናቋል። ከነጥባቸው መቀራረብ እና ኢትዮዽያ ቡና ማሸነፍ እና አቻ መውጣት የምድቡ አሸናፊ ሆኖ የሚያጠናቀቅበት በመሆኑ ከጨዋታው አስቀድሞ ጠንካራ ፉክክር እንደሚኖረው ተገመቶ ነበር። እንደተገመተው ሁሉ ሙሉ 90 ደቂቃውን በማራኪ እንቅስቃሴ ከበርካታ የጎል ሙከራ ጋር ታጅቦ በቀጠለው በዚህ ጨዋታ ጎል በማስቆጠር ቀዳሚ የነበሩት ባለ ሜዳዎቹ መከላከያዎች በሰለሞን ሞላ አማካኝነት ነበር። ብዙም ሳይቆይ የተገኘውን ፍ/ቅ/ምት ፍፁም ጥላሁን ወደ ጎልነት በመቀየር ኢትዮዽያ ቡናን አቻ ማድረግ ሲችል አምና በኢትዮዽያ ንግድ ባንክ ከ17 አመት በታች ፕሪምየር ሊግ ከፍተኛ ጎል አስቆጣሪ በመሆን የተሸለመው ተመስገን ዘውዱ ዘንድሮ ወደ ኢትዮዽያ ቡና ከተቀላቀለ ጀምሮ ጎል ማስቆጠሩን ቀጥሎበት ከእረፍት በፊት የግል ብቃቱን ተጠቅሞ ለኢትዮዽያ ቡና ሁለተኛ ጎል አስቆጥሮ በኢትዮዽያ ቡና 2-1 መሪነት እረፍት ወጥተዋል።

በሁለተኛው አጋማሽ በሁለቱ ቡድኖች በኩል ፉክክሩ አይሎ መከላከያ ወደ አቻ የተመለሱበትን ጎል በቅዱስ አስራት ማስቆጠር ሲችሉ ከጎሉ በኋላ የጨዋታ ብልጫ ወስደው ተጭነው መጫወት ቢችሉም ያገኙትን የጎል አጋጣሚ ሳይጠቀሙበት ቀርተዋል። ጨዋታው በአቻ ውጤት ተጠናቀቀ ሲባል ተቀይሮ የገባው ኪትካ ጃማ ከማዕዘን ምት የተሻገረለትን ኳስ በግንባሩ ገጭቶ ባስቆጠራት ጎል ጨዋታው በኢትዮዽያ ቡና 3 – 2 አሸናፊነት ተጠናቋል። ውጤቱን ተከትሎም ኢትዮዽያ ቡና የምድቡ አሸናፊ ሆኖ ማጠናቀቁን አረጋግጧል።

ሌሎች የምድብ ሀ ውጤቶች

የደረጃ ሰንጠረዥ

በምድብ ለ ሀዋሳ ከተማ የዚህ ሳምንት አራፊ ቡድን ቢሆንም ተከታዩ ወላይታ ድቻ ዛሬ ወደ ይርጋለም አቅንቶ በሲዳማ ቡና 1-0 በሆነ ውጤት በመሸነፉ ሀዋሳ ከተማ የምድብ ለ አሸናፊ ሆኖ ማጠናቀቁን አረጋግጧል።

የምድብ ለ ውጤቶች

የደረጃ ሰንጠረዥ