አቶ መኮንን ኩሩ በድጋሚ የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ቴክኒክ ዳሬክተር ሆነው ተመረጡ

በፌዴሬሽኑ መመዘኛ መሰረት አቶ መኮንን ኩሩ ተቋሙ የቴክኒክ ዳሬክተር ለመሆን የሚያበቃቸውን ውጤት አስመዝግበዋል፡፡

በኢትዮጵያ እግርኳሳዊ ልማት ላይ በርካታ ስራዎች ይሰራል ተብሎ የሚታመንበት የቴክኒክ ዳይሬክተር ቦታ ያለፈውን አንድ ዓመት ያለ ኃላፊነት ክፍት ሆኖ በመቅረቱ በርካታ መሰራት የሚገባቸው ስራዎች ተዘንግተው ቆይተዋል። አዲሱ የፌዴሬሽን በቦታው ሰው ለመቅጠር ባወጣው የቅጥር ማስታወቂያ መስፈርት መሰረትም የተወዳደሩ ግለሰቦች የፈተና ውጤት ታውቋል፡፡ በውጤቱም መሰረት በአራተኛ ደረጃ 17% በማምጣት አቶ እንዳለ ለገሰ ፣ በሦስተኛ ደረጃ 18% በማምጣት አቶ ግርማ ጥላሁን ፣ በሁለተኛ ደረጃ 38.1% በማምጣት አቶ ወንዲፍራው በቀለ የተቀመጡ ሲሆን 54.1% በማምጣት አንደኛ የወጡት አቶ መኮንን ኩሩ የኢትዮዽያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ቴክኒክ ዳሬክተር በመሆን ተሹመዋል።

አቶ መኮንን ኩሩ ከዚህ ቀደም ከህዳር ወር 2003 – የካቲት 2009 ድረስ ባሉት ስድስት ዓመታት በቴክኒክ ዳሬክተር ኃላፊነት ሲሰሩ የቆዩ ሲሆን ምክንያቱ ለጊዜው ባልታወቀ ምክንያት 2009 ላይ ራሳቸውን ከኃላፊነት ማንሳታቸው ይታወሳል ። አቶ መኮንን ኩሩ ወደ በድጋሚ ወደ ቦታው መመለሳቸውን እና በቀጣይ ሊሰሯቸው ያሰቡትን ዕቅድ አስመልክቶ በቀጣይ አንድ ዘገባ ይዘን የምንመለስ መሆኑን ከወዲሁ እንጠቁማለን ።