ቅድመ ዳሰሳ | ወላይታ ድቻ ከ መቐለ 70 እንደርታ

የጦና ንቦች የሊጉን መሪ የሚያስተናግዱበት ጨዋታን እንደሚከተለው ዳሰነዋል።

ከአስከፊ የውጤት ጉዞ በኋላ ባለፈው ሳምንት ወሳኝ የሜዳ ውጭ ድል በማሳካት የተነቃቁት የጦና ንቦች የሊጉን መሪ በሚያስተናግዱበት ጨዋታም ነጥብ ይዞ በመውጣት ከወራጅ ቀጠናው ለመራቅ አልመው ይገባሉ።

የወላይታ ድቻ ያለፉት 5 ጨዋታዎች አቋም (ከቅርብ ወደ ሩቅ)
አሸነፈ ተሸነፈ አቻ ተሸነፈ ተሸነፈ

ባለፈው ሳምንት በአሰልጣኝ ደለለኝ ደቻሳ እየተመሩ ጅማ አባ ጅፋርን ያሸነፉት ወላይታ ድቻዎች በዚ ጨዋታ ይዘውት የሚገቡትን አቀራረብ ለመገመት ቢከብድም ቡድኑ ከባለፈው ሳምንት አጨዋወት የተራራቀ ይሆናል ተብሎ አይገመትም። ቡድኑ የተጋጣሚን የማጥቂያ መንገድ ለመከላከል ከኋላ መስመሩ ላይ ለውጦች አድርጎ ወደ ጨዋታው መግባቱ አይቀሬ ነው።

ባለፈው ሳምንት ቡድን ጅማ አባጅፋር ባሸነፈት ጨዋታ ኳስን ተቆጣጥሮ በመስመሮች በሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ለማጥቃት ጥረት ያደረገ ሲሆን አማካዮቹ በረከት ወልዴ እና በዚህ ጨዋታ የቀድሞ ክለቡን የሚገጥመው ኢድሪስ ሰኢድ በጨዋታው ወሳኝ ሚና ነበራቸው። በዚህም አሰልጣኝ ዘለለኝ ደቻሳ በዚህ ጨዋታ ተመሳሳይ በኳስ ቁጥጥር ላይ የተመሰረተ እና በመስመሮች የግብ ዕድል ለመፍጠር የሚሞክር ቡድን ይዘው ይቀርባሉ ተብሎ ይጠበቃል።

ወላይታ ድቻዎች በጉዳት የሚያጡት ተጫዋች የለም። በአንፃሩ መኳንንት አሸናፊ እና ነጋሽ ታደሰ ከጉዳት ተመልሰዋል።

ተከታታይ ጨዋታዎች አሸንፈው የሊጉን አናት የተቆናጠጡት መቐለዎች በዚህ ዓመት ከሜዳ ውጪ ጥሩ ክብረወሰን ካላቸው ቡድኖች ይጠቀሳሉ። 

የመቐለ 70 እንደርታ ያለፉት 5 ጨዋታዎች አቋም (ከቅርብ ወደ ሩቅ)
አሸነፈ አሸነፈ አሸነፈ ተሸነፈ አሸነፈ

በቀጥተኛ አጨዋወት ውጤታማ የማጥቃት ጥምረት የፈጠሩት መቐለዎች በዚ ጨዋታም የተለመደው አጨዋወታቸው ይዘው ይገባሉ ተብሎ ሲጠበቅ ግዙፉ አጥቂ ኦኪኪ ኦፎላቢ ወደ ግብ ማስቆጠር መመለሱም የቡድኑ የማጥቃት ሀይል በብዙ መንገድ ያሻሽለዋል ተብሎ ይጠበቃል።

በተለይም ከዚህ በፊት በአማኑኤል ገብረሚካኤል የተንጠለጠለው የቡድኑ የግብ ማስቆጠር ድርሻ ናይጀርያዊው አጥቂ ወደ ግብ ማስቆጠሩ መመለሱ የክለቡ የግብ መጠን ከፍ ከማድረግ አልፎ ቡድኑ ከተገማቹ የማጥቃት አጨዋወት ወጥቶ ሌሎች አማራጮች እንዲሞክር በር ይከፍትለታል። በዚህም በተከታታይ ሦስት ጨዋታዎች ላይ ድል ያደረጉት መቐለዎች በአሰላለፋቸውም ሆነ በአጨዋወታቸው ላይ ለውጥ ያደርጋሉ ተብሎ አይጠበቅም። 

(በኤዲት የተካተተ፡ መቐለዎች ዋና አጥቂያቸው  አማኑኤልን በጉዳት አጥተዋል። በዚህ በዛሬው ጨዋታ በአሰላለፋቸው ላይ ለውጥ ያደርጋሉ ተብሎ ይጠበቃል። )

ምዓም አናብስት በዚህ ጨዋታ በረጅም ጊዜ ጉዳት ከሚገኘው ሚካኤል ደስታ እና አማኑኤልን በጉዳት ያጣሉ።

እርስ በርስ ግንኙነት

በሊጉ ለአራት ጊዜያት የተገናኙ ሲሆን መቐለ 3 በማሸነፍ የበላይነት አለው። ቀሪዋን ደግሞ ድቻ አሸንፏል። መቐለ 4 ሲያስቆጥር ድቻ አንድ አስቆጥሯል።

ግምታዊ አሰላለፍ

ወላይታ ድቻ (4-3-3)

መክብብ ደገፉ

ያሬድ ዳዊት – ደጉ ደበበ – አንተነህ ጉግሳ – እዮብ ዓለማየሁ

እድሪስ ሰይድ ተስፋዬ አለባቸው – በረከት ወልዴ

ቸርነት ጉግሳ – ባዬ ገዛኸኝ – ፀጋዬ ብርሀኑ

መቐለ 70 እንደርታ (4-4-2)

ፍሊፕ ኦቮኖ

ሥዩም ተስፋዬ – ላውረንስ ኤድዋርድ – አሌክስ ተሰማ – አንተነህ ገብረክርስቶስ

ዮናስ ገረመው – ዳንኤል ደምሴ – ሙሉጌታ ወልደጊዮርጊስ – ሳሙኤል ሳሊሶ

ያሬድ ከበደ – ኦኪኪ ኦፎላቢ


© ሶከር ኢትዮጵያ