‹‹ የኢንፋንቲኖ ጉብኝት የተሳካ ነበር›› የኢእፌ ፕሬዝዳንት አቶ ጁነይዲ ባሻ

አዲሱ የፊፋ ፕሬዝዳንት ጂያኒ ኢንፋንቲኖ ላንት ምሽት አዲስ አበባ ገብተው የተለያዩ ክንውኖችን በማከናወን ዛሬ ረፋድ ላይ ኢትዮጵያን ለቀዋል፡፡

ኢንፋንቲኖ ትላንት በደቡብ ሱዳን ጁባ በነበራቸው የጥቂት ሰአታት ቆይታ የደቡብ ሱዳን እና ቤኑን ጨዋታን ተመልክተው እንዲሁም በፊፋ ድጋፍ የተሰራው የሃገሪቱ እግርኳስ ፌዴሬሽን ህንፃን በመመረቅ ካሳለፉ በኋላ ምሽት 2፡30 ገደማ አዲስ አበባ ገብተዋል፡፡

PicsArt_1458822517112

በፊፋ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ወቅት የድምፅ ቆጠራ ላይ ተሳትፎ ያደረጉት የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት አቶ ጁነይዲ ባሻ ከሶከር ኢትዮጵያ ጋር ባደረጉት ቆይታ የኢንፋንቲኖ ወደ ሃገራችን መምጣት ምክንያት ያስረዳሉ፡፡

‹‹ኢትዮጵያ የአፍሪካ እግርኳስን በቀደምትነት ከመሰረቱ ሀገሮች አንዷ በመሆኗ ፣ የአፍሪካ ህብረት መቀመጨ በመሆኗ ፣ የእግርኳስ መሰረተ ልማቶች በማስፋፋት ላይ የምትገኝ በመሆኗ እና በፊፋ ምርጫ ወቅት በነበረን ተሳትፎ ምክንያት እንዲሁም ከእኛ በቀረበላቸው ጥያቄ መሰረት ነበር የመጡት፡፡›› ይላሉ፡፡ ፕሬዝዳንቱ አክለውም በተደረገላቸው አቀባበል እና በቆይታቸው ደስተና መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

‹‹ በአቀባበላችን ባደረግንላቸው መስተንግዶ በጣም ደስተኛ ነበሩ፡፡ ባረፉበት ሸራተን አዲስ ልደታቸውን አክብረንላቸዋል፡፡ በአጠቃላይ በነበራቸው አጭር ቆይታ በጣም ደስተኛ ነበሩ፡፡›› ብለዋል፡፡

ጂያኒ ኢንፋንቲኖ በቆይታቸው ፌዴሬሽኑ ያሰባቸውን ነገሮች መከወኑንና ቆይታቸው የተሳካ እንደነበር ገልፀዋል፡፡

‹‹ ፕሬዝዳንቱ ኢትዮጵያ እንደሚመጡ ካረጋገጥንበት እለት ጀምሮ በደንብ ተዘጋጅተን የጠበቅናቸው በመሆኑ በሊግ አወቃቀር ፣ በታዳጊዎች ልማት እና ሌሎች ወደ 9 በሚጠጉ ጉዳዮች ዙርያ ውይይት አድርገናል፡፡ በአቅም ግንባታ ድጋፍ እንዲያደርጉልን ውይይት ያደረግን ሲሆን እርሳቸውም ለኢትዮጵያ እግርኳስ የነበራቸው ግምት እንደተቀየረና ድጋፍ እንደሚያደርጉም አሳውቀዋል፡፡

‹‹ ጉብኝታቸው እጅግ የተሳካ ነበር፡፡ ፊፋ ድጋፍ እንዲያደርግልን በምንፈልጋቸው ጉዳዮች ላይ ውይይት አድርገናል፡፡ እርሳቸውም ድጋፍ እንደሚያደርጉ በመግለጽ ከወራት በኋላ በድጋሚ ተመልሰው እንደሚመጡ ቃል ገብተውልናል፡፡ ››

PicsArt_1458822743815 PicsArt_1458822934838

የ46 አመቱ ጂያኒ ኢንፋንቲኖ አዲስ አበባ ከገቡ በኋላ ትላንት ምሽት ከወጣቶች እና ስፖርት ሚኒስቴር ሚኒስትር አቶ ሬድዋን ሁሴን ጋር የተወያዩ ሲሆን ባረፉበት ሸራተን አዲስ የእራት ግብዣ ተደርጎላቸዋል፡፡ የተዘጋጀላቸውን ልዩ ኬክ በመቁረስም የ46ኛ አመት የልደት በአላቸውን አክብረዋል፡፡

ዛሬ ጠዋት ደግሞ የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ጽህፈት ቤት እና የወጣቶች ስፖርት አካዳሚን የጎበኙ ሲሆን በዚህ አመት መጨረሻ ተመልሰው በመምጣት ኢትዮጵያን በስፋት ለመቆብኘት እንዳቀዱ በመግለፅ ረፋድ 4፡00 ገደማ ኢትዮጵያን ለቀዋል፡፡

PicsArt_1458822627771

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *