ግዙፉ ተከላካይ መከላከያን ተቀላቅሏል

ከሰዓታት በፊት አምሳሉ ጥላሁንን ያስፈረሙት መከላከያዎች ቶማስ ስምረቱንም ወደ ስብስባቸው መቀላቀላቸውን ሶከር ኢትዮጵያ አውቃለች።

በአዲስ መልክ ስብስቡን እያጠናከረ የሚገኘው መከላከያ እስካሁን ተስፋዬ አለባቸው፣ በረከት ደስታ፣ ከነዓን ማርክነህ፣ ፍፁም ዓለሙ፣ ሳሙኤል ሳሊሶ፣ ዳግም ተፈራ፣ ምንይሉ ወንድሙ እና አምሳሉ ጥላሁንን ያስፈረመ ሲሆን የአሌክስ ተሰማ፣ ኢብራሔም ሁሴን፣ ግሩም ሀጎስ እና ዳዊት ማሞን ውልም ለተጨማሪ ዓመት ማደሱ ይታወቃል። አሁን ባገኘነው መረጃ መሠረት ደግሞ ግዙፉ የመሐል ተከላካይ ቶማስ ስምረቱ የቡድኑ ዘጠነኛ ፈራሚ ሆኗል።

ከስፖርት ቤተሰብ የተገኘው የቀድሞ የሱሉልታ፣ ወላይታ ዲቻ፣ ኢትዮጵያ ቡና እና ወልቂጤ ከተማ ተጫዋች የተጠናቀቀውን የውድድር ዓመት በአዳማ ከተማ አሳልፎ ነበር። አሁን ደግሞ በአዳማ አብሮት ከሰራው አሠልጣኝ ፋሲል ተካልኝ ጋር በድጋሜ ለመስራት ጦሩን በአንድ ዓመት ውል ተቀላቅሏል።