በኢንተርናሽናል ጨዋታ ምክንያት ተቋርጦ የቆየው የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ ዛሬ ሲጀምር መከላከያ ድል ቀንቶታል፡፡ ወላይታ ድቻም ግቡን ሳያስደፍር መውጣቱን ቀጥሏል፡፡
በ09፡00 ወላይታ ድቻን ያስተናገደው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ካለ ግብ አቻ ተለያይቷል፡፡ ጨዋታው ቀዝቃዛ እንቅስቃሴ የታየበት ሲሆን እምብዛም የግብ ሙከራዎች ያልታዩበት ሆኖ ተጠናቋል፡፡ ወጤቱ በደረጃ ሰንጠረዡ ላይ ለውጥ ባያስከትልም ወላይታ ድቻ ሁለተኛው ዙር ከተጀመረ ጀምሮ ግቡን ሳያስደፍር የወጣበት ሆኖ ተመዝግቧል፡፡
በ11፡30 መከላከያ ሀዲያ ሆሳዕናን አስተናግዶ 2-1 በማሸነፍ ከመውረድ ስጋት መጠነኛ እፎይታ አግኝቷል፡፡ ጦሩ በሃይሉ ግርማ ባስቆጠረው ግሩም ግብ የመጀመርያውን አጋማሽ በመሪነት ሲያጠናቅቅ በሁለተኛው አጋማሽ እጅግ ተሸሽለው የቀረቡት ሃድያ ሆሳዕናዎች በሀይደር ሸረፋ አማካኝነት አቻ መሆን ችለው ነበር፡፡ ከግቡ መቆጠር በኋላ ሀድያዎች ተጨማሪ ግብ ለማግኘት ጫና ፈጥረው ቢንቀሳቀሱም በ79ኛው ደቂቃ ተከላካዩ ቴዎድሮስ በቀለ በቅጣት ምት አስቆጥሮ መከላከያን ለድል አብቅቷል፡፡
ሊጉ ነገ እና ከነገ በስቲያ ሲቀጥል ነገ በ09፡00 ቅዱስ ጊዮርጊስ ከ አርባምንጭ ከተማ (አአ) ፣ አዳማ ከተማ ከ ድሬዳዋ ከተማ (አዳማ) ይጫወሉ፡፡ 11፡30 ላይ ደግሞ ደደቢት ከ ዳሽን ቢራ ይፋለማሉ፡፡