ፋሲል ከተማ የደደቢቱ አጥቂ አቤል ያለውን በውሰት ውል ማስፈረሙ ታውቋል፡፡ በውድድር አመቱ ተስፋ ሰጪ እንቅስቃሴ ያሳየው አቤል እስከ ውድድር ዘመኑ ማብቂያ የፋሲልን ማልያ ለብሶ የሚጫወትም ይሆናል፡፡
የሐረር ሲቲ ከ17 አመት በታች ቡድንን ለቆ ዘንድሮ ደደቢትን የተቀላቀለው አቤል በፍጥነት ዋናውን ቡድን ተቀላቅሎ በተለይም በአአ ከተማ ዋንጫ ድንቅ እንቅስቃሴ ማሳየት ችሎ ነበር፡፡ በፕሪምየር ሊጉም ተቀይሮ በመግባት ጨዋታዎችን ማድረግ ችሏል፡፡
ከፋሲል ጋር በተያያዘ ዜና ከከፍተኛ ሊግ ክለቦች ተጫዋቾችን ለማስፈረም እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡ የቡድኑ አሰልጣኝ ዘማርያም ወልደጊዮርጊስ ባለፈው ሳምንት ለሶከር ኢትዮጵያ በሰጡት አስተያየት ለቡድኑ የሚያስፈልጉ ተጫዋቾችን ለመመልመል የከፍተኛ ሊግ ጨዋታዎችን እየተመለከቱ እንደሆነ መግለጻቸው የሚታወስ ነው፡፡