ሳሙኤል ሳኑሚ ወደ ግብፅ ሊያመራ ይችላል

ባሳለፍነው የውድድር ዘመን በ22 ግቦች የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ኮኮብ ግብ አግቢ የነበረው ናይጄሪዊው ሳሙኤል ሳኑሚ ወደ ግብፁ አል-መስሪ በአሁን ክረምት ሊዘዋወር እንደሆነ ተነግሯል፡፡ ፈጣኑ የመስመር ተጫዋች ሳኑሚ በአል መስሪ የሙከራ ግዜ ያሳለፈ ሲሆን አንደ ወኪሉ አብዱልራህማን መግዲ ገለፃ ከሆነ ሙከራው የተሳካ ነበር፡፡

የሳላዲን ሰዒድን እና ሽመልስ በቀለ ወኪል የሆነው መግዲ ስለጉዳዩ ለሶከር ኢትዮጵያ በሰጠው አስተያየት “አሁን መናገር እችላለው ሳሙኤል ሳኑሚ በአል-መስሪ የነበረውን የሙከራ ግዜ በተሳከ ሁኔታ አጠናቅቋል፡፡ አል-መስሪ ለደደቢት የዝውውር ጥያቄ ለማቅረብ ፍላጎት አለው፡፡” ብለዋል፡፡

አንድ የውድድር ዓመትን ብቻ በሰማያዊ ጦሮቹ ያሳለፈው ሳኑሚ በቀጣዮቹ ጥቂት ቀናት የአል መስሪ ንብረት መሆኑ አይቀሬ እንደሆነ መግዲ ጨምረው ተናግረዋል፡፡ “በቀጣዮቹ ጥቂት ቀናት ወደ አዲስ አበባ መጥቼ ዝውውሩን እንጨርሳለን፡፡” በሚል አስተያየተቸውን ሰጥተዋል፡፡

በኢትዮጵያ ለመብራት ሐይል (ኤሌክትሪክ)፣ ቅዱስ ጊዮርጊስ እና ደደቢት የተጫወተው ሳሙኤል ሳኑሚ 1 ግዜ የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ አሸናፊ ነው፡፡