ጋቶች ፓኖም በዚህ ሳምንት ጨዋታ ላይ አይሰለፍም

በፕሪምየር ሊጉ ከፍተኛ በሆነ የዝውውር ሂሳብ መቐለ ከተማን የተቀላቀለው ጋቶች ፓኖም ያለፉትን አምስት ቀናት ባጋጠመው የጡንቻ መሳሳብ ጉዳት ምክንያት ልምምድ እየሰራ እንዳልሆነ ከክለቡ አካባቢ ያገኘነው መረጃ ያሳያል።

ይህን ተከትሎ ጉዳቱ በቂ የማገገሚያ ጊዜ የሚያስፈልገው በመሆኑ ጋቶች ፓኖም በኢትዮዽያ ፕሪምየር ሊግ ሁለተኛው ዙር የመጀመርያ ጨዋታ መቐለ ከተማ በሜዳው ከአርባምንጭ ከተማ ጋር ሲያደርግ እንደማይሰለፍ ተረጋግጧል። ተጫዋቹ ከጉዳቱ አገግሞ መቼ ወደ ሜዳ እንደሚመለስ ማረጋገጫ ያልተሰጠ ቢሆንም በቀጣይ ሳምንት መቐለ ከተማ ከወልዋሎ በሚያደርገው ጨዋታ ላይ ሊደርስ እንደሚችል ተነግሯል።
ባለፈው ክረምት ኢትዮዽያ ቡናን ለቆ ወደ ሩስያው ክለብ አንዚ ማካቻካላ ያመራው ጋቶች የተጠበቀውን ያህል የመሰለፍ እድል ባለማግኘቱ በስምምነት ተለያይቶ ወደ ሀገር ቤት የተመለሰ ሲሆን በደቡብ አፍሪካው ቤድቬስት ዊትስ የሙከራ ጊዜውን አሳልፎ ከተመለሰበት ማግስት ጀምሮ ወደ አሳዳጊ ክለቡ ኢትዮዽያ ቡና ይመለሳል ቢባልም ለፕሪምየር ሊጉ አዲስ ለሆነው መቐለ ከተማን ፊርማውን ማኖሩ የሚታወስ ነው።

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *