ለሳምንታት ካለውጤት ዘልቆ የቆየው የዳዊት እስጢፋኖስ እና የኢትዮጵያ ቡና ድርድር በመጨረሻም በኮንትራት ማራዘምያ ስምምነት ተቋጭቷል፡፡ ዳዊት ከክለቡ ከፍተኛ ገንዘብ በመጠየቁ የፊርማው ሂደት የዘገየ ሲሆን ተጫዋቾች እየለቀቁበት ለሚገኘው ኢትዮጵያ ቡና የአምበሉ መፈረም እፎይታን አስገኝቶላቸዋል፡፡
ክለቡ በይፋዊ የፌስቡክ ገፁ የዳዊትን መፈረም ዜና እንዲህ ባለ መልኩ ይፋ አድርጓል፡-
‹‹
በ2006 ዓ.ም ኢትዮጵያ ቡናን በአምበልነት እየመራ ምርጥ የመሃል ሜዳ እንቅስቃሴ በማድረግ በርግጥም ብቃቱን አስመስክሯል ፡፡ ከዚህ ውጪ አሁንም የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ተጫዋች ውስጥ ተካቶ ይገኛል ፡፡ ክለቡን ዘንድሮም በተገቢው ሁኔታ እያገለገለ የሚገኘው ዳዊት በሊጉ በባንክ ፣ በመድን ፣ በመከላከያ ፣ በዳሽን እና በደደቢት መረብ ላይ ጎሎችን ያሳረፈ ሲሆን በተለይ ዘንድሮ በቅጣት ምት ያስቆጠራቸው ጎሎች የቅጣት ምት መቺነቱንም እያስመሰከሩ ነው ፡፡
በደጋፊው ዘንድ ከፍተኛ ተወዳጅነት ያለው ዳዊት እስጢፋኖስ ዛሬ ከክለቡ ቦርድ አመራሮች ጋር ባደረገው ውይይት ለቀጣይ ሁለት አመታትም ከክለቡ ጋር ለመቆየት ተስማምቷል ፡፡ ዛሬ ውሉንም አድሷል ፡፡
››