አንደኛ ሊግ | ወደ ሩብ ፍፃሜ ያለፉ ቡድኖች ሲታወቁ ሐሙስ ወሳኞቹ ጨዋታዎች ይደረጋሉ

የኢትዮጵያ አንደኛ ሊግ የምድብ ጨዋታዎች ዛሬ ተደርገው ሲጠናቀቁ ወደ ሩብ ፍፃሜ የተሸጋገሩ ክለቦች በሙሉ ታውቀዋል። ወደ ከፍተኛ ሊግ በቀጥታ ለማለፍም ሐሙስ ይፋለማሉ።

በባቱ ከተማ እየተካሄደ በሚገኘው በዚህ የማጠቃለያ ውድድር ትላንት ሊደረጉ የነበሩት የምድብ ሀ እና ለ የመጨረሻ ጨዋታዎች በዝናብ ምክንያት ወደ ዛሬ ተሸጋግረው የተካሄዱ ሲሆን በምድብ ሀ ኮልፌ ቀራኒዮ ላስታ ላሊበላን 2-0፣ አዲስ አበባ ፖሊስ ጎፋ ባሬንቼን 1-0 አሸንፈዋል። በዚህም መሠረት አአ ፖሊስ በ10 ነጥቦች ቀዳሚ ሆኖ ወደ ሩብ ፍፃሜ ሲያልፍ ኮልፌ ቀራኒዮ በ7 ነጥቦች ተከትሎት አልፏል።

በምድብ ለ መቱ ከተማ ዳሞት ከተማን 2-0 ቢያሸንፍም ተያይዘው ከምድቡ መሰናበታቸውን አረጋግጠዋል። ጋሞ ጨንቻ ደግሞ ራያ አዘቦን 4-0 በመርታት ነጥቡን 10 አድርሶ በ9 ነጥቦች አስቀድሞ ማለፉን ያረጋገጠው ቂርቆስ አስከትሎ ሩብ ፍፃሜውን ተቀላቅሏል።

እሁድ እለት የምድብ ሐ እና መ ጨዋታዎች የተጠናቀቁ ሲሆን ባቱ ከተማ እና ሱሉልታ ከተማ ከምድብ ሐ፣ ሰሜን ሸዋ ደብረብርሀን እና ሰሎዳ ዓድዋ ደግሞ ከምድብ መ በቅደም ተከተል አንደኛ እና ሁለተኛ ሆነው ወደ ሩብ ፍፃሜ አልፈዋል።

የሩብ ፍፃሜ ጨዋታዎች ሐሙስ የሚደረጉ ሲሆን አሸናፊዎቹ አራት ቡድኖች በቀጥታ ወደ ከፍተኛ ሊግ ማደረጋቸውን የሚያረጋጥጡ ይሆናል። ተሸናፊዎቹ አራት ቡድኖች ደግሞ ቅዳሜ ዕለት በሚያደርጉት የመለያ ጨዋታ የሚያሸንፉ ሁለት ቡድኖች 5ኛ እና 6 ሀላፊ ሆነው ከፍተኛ ሊጉን ይቀላቀላሉ።

የሩብ ፍፃሜ መርሐ ግብር
ሐሙስ
ሐምሌ 18 ቀን 2011

3:00
| አአ ፖሊስ ከ ሰሎዳ ዓድዋ (ጨዋታ 1)

5:00
| ኮልፌ ቀራኒዮ ከ ሰ/ሸ/ደ/ብርሀን (ጨዋታ 2)

7:00
| ጋሞ ጨንቻ ከ ሱሉልታ ከተማ (ጨዋታ 3)

9:00
| ቂርቆስ ከ ባቱ ከተማ (ጨዋታ 4)

የመለያ ጨዋታዎች
ቅዳሜ ሐምሌ 20 ቀን 2011
3:00|
ጨዋታ 1 ተሸናፊ ከ ጨዋታ 2 ተሸናፊ

5:00|
ጨዋታ 3 ተሸናፊ ከ ጨዋታ 4 ተሸናፊ

*ማስታወሻ – ሁሉም ጨዋታዎች በሼር ሜዳ ይደረጋሉ


© ሶከር ኢትዮጵያ

በድረ-ገጻችን ላይ የሚወጡ ጽሁፎች ምንጭ ካልተጠቀሱ በቀር የሶከር ኢትዮጵያ ናቸው፡፡ እባክዎ መረጃዎቻችንን በሚጠቀሙበት ወቅት ምንጭ መጥቀስዎን አይዘንጉ፡፡