የባህር ዳር ከተማ ወሳኝ ተጨዋች ወደ ሜዳ ተመልሷል

በጉዳት ላይ ከሚገኙት ሦስቱ የጣናው ሞገድ ተጫዋቾች መካከል አንዱ የሆነው ተጨዋች ወደ ሜዳ ተመልሷል።

በዘንድር የውድድር ዓመት ከፋሲል ከነማ ወደ ባህር ዳር ከተማ በማቅናት ድንቅ እንቅስቃሴ እያደረገ የሚገኘው ፍፁም ዓለሙ ደረቱ ላይ በደረሰ ጉዳት ከሜዳ መራቁ ይታወሳል። ቡድኑ ባህርዳር ወደ ሃዋሳ አምርቶ በሲዳማ ቡና ሲሸነፍ ከስብስቡ ውጪ የነበረው ተጨዋቹ ትላንት እና ዛሬ ከቡድን አጋሮቹ ጋር በመሆን ልምምድ እንደሰራ ታውቋል። ባህር ዳር ከተማ ነገ በሜዳው ወልዋሎን በሚጋብዝበት ጨዋታ ወደ ሜዳ ገብቶ ቡድኑን እንደሚያገለግል ተጠቁሟል።

በተያያዘ ዜና በጉዳት ላይ የሚገኙት ወሰኑ ዓሊ እና አቤል ውዱ አሁንም ከጉዳታቸው እንዳላገገሙ ተነግሯል። በተለይ ፈጣኑ የመስመር አጥቂ ወሰኑ ከደረቱ በታች በሚገኘው አካሉ ላይ በደረሰበት ጉዳት ምክንያት ለ1 ወር ከሜዳ እንደሚርቅ ተገልጿል። ግዙፉ የተከላካይ መስመር ተጨዋች አቤል በበኩሉ አንገቱ ላይ ካጋጠመው ጉዳት እያገገመ እንደሆነ እና ምናልባት ከ1 ሳምንት በኋላ ወደ ሜዳ እንደሚመለስ ታውቋል።

©ሶከር ኢትዮጵያ