አሰልጣኝ ሳምሶን አየለ ወዴት?

ከስሑል ሽረ አሰልጣኝነት ለመልቀቅ ደብዳቤ ያስገቡት ሳምሶን አየለ ቀጣይ ሁኔታ ከነገ በኋላ ይታወቃል።

ባለፈው የውድድር ዓመት አጋማሽ ስሑል ሽረን ለማሰልጠን ተስማምተው ቡድኑ በፕሪምየር ሊጉ እንዲቆይ ያስቻሉት አሰልጣኝ ሳምሶን አየለ ከጥቂት ቀናት በፊት ለቡድናቸው ስሑል ሽረ የልቀቁኝ ደብዳቤ ማስገባታቸው ይታወሳል።

ምንም እንኳ አሰልጣኙ የመልቀቅያ ደብዳቤ ቢያስገቡም ቡድናቸው ስሑል ሽረ አሰልጣኙን ለማነጋገር እና በክለቡ የሚቆዩበት ሁኔታ ለማመቻቸት በነገው ዕለት በክለቡ ፅሕፈት ቤት እንዲገኙ በይፋዊ ደብዳቤ ገልጿል። በሌላ በኩል ደግሞ አዲስ አሰልጣኝ ለመቅጠር በእንቅስቃሴ ላይ የሚገኙት ወልዋሎዎች የአሰልጣኙ ፈላጊ ሆነው ብቅ እንዳሉ እየተሰማ ይገኛል።

ከወልዋሎ በተጨማሪ ከአንድ የፕሪምየር ሊግ ክለብ ጋርም ስማቸው እየተነሳ የሚገኘት አሰልጣኝ ሳምሶን አየለ በቀጣይ ቀናት ከስሑል ሽረ ይቀጥላሉ ወይስ ወደ አዲስ ክለብ ይቀላቀላሉ የሚል ጥያቄ ምላሽ ያገኛል።

© ሶከር ኢትዮጵያ