ሽመልስ በቀለ በተከታታይ ጨዋታዎች ቡድኑን ባለድል አድርጓል

በግብፅ ፕሪምየር ሊግ 14ኛ ሳምንት ምስር ለል ማቃሳ ሲያሸንፍ ሽመልስ በቀለ ለሁለተኛ ተከታታይ ጨዋታ ቡድኑን አሸናፊ ያደረገ ጎል አስቆጥሯል።

በካይሮ አረብ ኮንትራክተርስ ስታዲየም አዲስ አዳጊው ናሽናል ባንክ ኦፍ ኢጂብትን የገጠመው ምስር ለል ማቃሳ 1-0 በሆነ ውጤት በማሸነፍ ደረጃውን ወደ አራተኛ ከፍ ማድረግ የቻለበትን ድል ማስመዝገብ ችሏል። የቡድኑን ብቸኛ ጎልም ኢትዮጵያዊው አማካይ ሽመልስ በቀለ በ28ኛው ደቂቃ አስቆጥሯል።

ባለፈው ሳምንት ምስር ለል ማቃሳ ከአምስት ተከታታይ ድል አልባ ጨዋታ በኋላ ኤል ኤንታግ ኤል አርቢን 1-0 አሸንፎ ወደ ድል ሲመለስም ብቸኛዋን ጎል አስቆጥሮ የነበረው ሽመልስ በውድድር ዓመቱ ያስቆጠራቸውን ጎሎች አምስት በማድረስ በጎል አስቆጣሪዎት ፉክክር ውስጥ መካተት ችሏል።


© ሶከር ኢትዮጵያ