የሴካፋ ውድድር ዝግጅት ተገመገመ

በኢትዮጵያ አስተናጋጅነት የሚካሄደው የምስራቅእና መካከለኛው አፍሪካ ሀገራት ከ23 ዓመት በታች ውድድር ወቅታዊ የዝግጅት ሁኔታ መገምገሙን ፌዴሬሽኑ አስታውቋል።

የፌዴሬሽኑ መረጃ ይህንን ይመስላል:-

የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ትናንት ሰኔ 1/2013 ባደረገው አስቸኳይ ስብሰባ የፊታችን ሰኔ 26/2013 በባህር ዳር የሚጀመረው የሴካፋ ከ23 ዓመት በታች ውድድር ቅድመ ዝግጅት ያለበት ደረጃን ገምግሟል።

ለሴካፋ ውድድር የተዘጋጀው የውድድር ማስፈጸሚያ ሰነድ የቀረበ ሲሆን፤ የተወሰኑ ማሻሻያዎች ተደርገውበት ወደ ስራ እንዲገባ ተወስኗል።

የሴካፋ ውድድር ብሔራዊ አብይ ኮሚቴ ከፌደራል መስሪያ ቤቶች ከኢፌዲሪ ባህል እና ቱሪዝም ሚኒስቴር ፣ከኢፌዲሪ ስፖርት ኮሚሽን፣ ከኢፌዲሪ ሰላም ሚኒስቴር ፣ የኢፌዲሪ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ ኢትዮ ቴሌኮም እና የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዳሬሽን ፕሬዝዳንት የተካተቱበት አብይ ኮሚቴ ተዋቅሯል።

በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ስራ አመራር ኮሚቴ አባል እና የማርኬቲንግ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ አበበ ገላጋይ የሴካፋ ዝግጅት Local Organizing Committee ሰብሳቢ ሆነው የተሰየሙ ሲሆን በስራቸውም 8 ልዩ ልዩ ንዑሳን ኮሚቴዎች ተዋቅረው ወደ ስራ ገብተዋል። ንዑሳን ኮሚቴዎች የሚከተሉት ሲሆኑ የእያንዳንዱ ንዑስ ኮሚቴ ሰብሳቢ የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ናቸው። (ማርኬቲንግ እና ስፖንሰር ሺፕ፣ ፕሮቶኮል እና አኮሞዴሽን ና ትራንስፖርት፣ የሜዳ እና ሎጂስቲክ ዝግጅት፣ የጸጥታ ኮሚቴ፣ ሚዲያ አክሪዲቴሽን ኮሚቴ፣ ህክምና ኮሚቴ፣ የባህል እና መዝናኛ ኮሚቴ)

በዚህ የሴካፋ ውድድር የሚያስፈልጉ በጀቶች ከመንግስት፣ ከስፖንሰር እና ከሴካፋ የሚገኙ ናቸው። ከመንግስት የሚያስፈልገው ተጨማሪ በጀት ቀደም ሲል ለሚመለከተው አካል ቀርቧል።