​ጅማ አባ ጅፋር ጋናዊ አማካይ አስፈረመ

አዲሱ የፕሪምየር ሊግ ክለብ ጅማ አባ ጅፋር ጋናዊው የአጥቂ አማካይ አሚኑ መሐመድን አስፈርሟል፡፡

የ28 አመቱ አሚን በሀገሩ ክለብ ሪል ታሚል መጫወት ጀምሮ በአሻንቲ ጎልድ እና አሻንቲ ኮቶኮ ክለቦች አሳልፏል፡፡ ወደ ጅማ ከማምራቱ በፊት በነበሩ 3 የውድድር ዘመናት ደግሞ ለቤከም ዩናይትድ ሲጫወት ቆይቷል፡፡

አሰልጣኝ ገብረመድህን ኃይሌ ቡድኑን በአዲስ መልኩ እያዋቀሩ የሚገኙ ሲሆን በሁሉም የሜዳ ክፍሎች በርካታ አዳዲስ ተጫዋቶችን ማስፈረማቸውን ቀጥለው ከዳንኤል ኦጄ (ጋና/ግብ ጠባቂ) እና ሲሶኮ አዳማ (ማሊ/ተከላካይ) በመቀጠል አማካዩ አሚኑን አስፈርመዋል፡፡ በቀጣይ ጊዜያትም ከናይጄርያ እና ጋና ሁለት የአጥቂ መስመር ተጫዋቾችን ለማስፈረም እየተንቀሳቀሱ እንደሆነ ታውቋል፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *