“ጥንቃቄ በተሞላበት መንገድ በትኩረት እንጫወታለን ፤ ጨዋታው በሜዳችን ስለሆነ ከፍተህ አትጫወትም” ዘሪሁን ሸንገታ

በነገው ዕለት ከዛንዚባሩ ኬኤምኬኤም ጋር የቻምፒየንስ ሊግ የማጣሪያ የመልስ ጨዋታ ያለው የቅዱስ ጊዮርጊሱ ዋና አሠልጣኝ ዘሪሁን ሸንገታ ከጨዋታው በፊት ሀሳባቸውን ሰጥተውናል።

ስለ ዝግጅት…

ዝግጅት ጥሩ ነው። ከጨዋታው መልስ የተወሰነ እረፍት አድርገን ዝግጅታችን በጥሩ መንገድ አድርገናል። በሜዳችን ካለፈው ጨዋታ የተሻለ ነገር ለማድረግ ተዘጋጅተናል።

ስለ ነገው ጨዋታ…

ጥንቃቄ በተሞላበት መንገድ በትኩረት እንጫወታለን። ጨዋታው በሜዳችን ስለሆነ ከፍተህ አትጫወትም ፤ የተሻለ ነገር ለማድረግ እንሰራለን። በሜዳችን ነው እና በምናውቀው አየር ፀባይ ነው የምንጫወተው። የተሻለ ነገር ለመስራት ዝግጅታችን ጨርሰናል።

ስለ አዳዲስ ተጫዋቾች…

አራት ተጫዋቾች መጥተዋል። የወጡት አስር፣ አስራ አንድ ተጫዋቾች ናቸው ፤ ትላልቅ ተጫዋቾች ናቸው። በእነሱ ምትክ አራት ተጫዋቾች አስፈርመናል ፤ ከቡድኑ ጋር ተዋህደዋል ወይ ለሚለው ግን ገና ናቸው። ጨዋታዎች አድርገውም ወደ ሪትማቸው ላይመጡ ይችላሉ። ባላቸው ብቃት ከቡድኑ ጋር ለማዋሀድ እየሰራንበት ነው።

ጨዋታው በዝግ መሆኑ…

ደጋፊያችን ጉልበታችን ነው። ደጋፊዎቻችን ባሉበት ያማረ ጨዋታ ነው የምንጫወተው። አሁን ግን የሉም ፤ ሜዳው ለሁለታችንም አንድ አይነት ነው የሚሆነው ማለት ነው። ግን ከሜዳችን ውጭ ጥሩ ነገር ይዘን መጥተናል ፤ ይሄ ነገር ሳናስብ ጠንክረን በመጫወት ውጤት ይዘን እንወጣለን።

በውድድሩ ረጅምር ርቀት ስለመጓዝ…

መጀመርያ ስለ ነገው ጨዋታ ነው የምናሰበው ፤ ለነገው ጨዋታም በቂ ዝግጅት አድርገናል። በሀገራችን ነው የምጫወተው የተሻለ ነገር ሰርተን ለሀገራችንም ለጊዮርጊስም ከፍ ያለ ነገር ለማድረግ ተዘገጅተናል። ስለ ቀጣይ ግን የዛኔ ብንነጋገር ደስ ይለኛል።