ከፍተኛ ሊግ | ጅማ አባቡና አዲስ አሰልጣኝ ቀጥሯል

የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ ተወዳዳሪው ጅማ አባ ቡና ዳዊት ሀብታሙን በአሰልጣኝነት ሾሟል።

በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ላይ የአንድ ዓመት የተሳትፎ ታሪክ ያለው ጅማ አባ ቡና ያለፉትን ስድስት ዓመታት በከፍተኛ ሊጉ ላይ እየተወዳደረ ዘንድሮም በምድብ ሀ ስር ተደልድሎ ይገኛል። ቡድኑ የውድድር ዓመቱን በአሰልጣኝ ይስሀቅ ረጋሳ መሪነት ቢጀምርም በተከታታይ አምስት ጨዋታዎች ሽንፈት ማስተናገዱን ተከትሎ አሰልጣኙ ከክለቡ የተለያዩ ሲሆን ያለፉትን አስራ ሁለት ቀናቶች ቡድኑን ልምምድ ሲያሰራ የነበረው እና እንዲሁም ሁለት ጨዋታዎችን አንዳንድ የወረቀት ጉዳዮች ባለመጠናቀቃቸው የተነሳ መምራት ሳይችል የቀረው አሰልጣኝ ዳዊት ሀብታሙ በዛሬው ዕለት በይፋ የቡድኑ ዋና አሰልጣኝ በመሆን ተሹሟል።

የቀድሞው የለገጣፎ ለገዳዲ ሀምበሪቾ እንዲሁም ደግሞ በወላይታ ድቻ እና በወልቂጤ ከተማ ረዳት አሰልጣኝ ሆኖ ያገለገለው አሰልጣኝ ዳዊት እስከ ዓመቱ መጨረሻ ድረስ ቡድኑን እየመራ የሚቆይ ይሆናል።