የካፍ ፕሬዝዳንት እስር እና ሌሎች የአፍሪካ እግርኳስ መረጃዎች

የካፍ ፕሬዚዳንት እስር

ባለፈው ዓመት የካፍ ፕሬዚደንት ሆነው የተመረጡት ማዳጋስካራዊ አህመድ አህመድ በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው በፓሪስ ፖሊስ ቁጥጥር ውለዋል። የፊፋ ስብስባ ለመገኘት ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ወደ ፓሪስ ያመሩት ፕሬዝደንቱ ከስብሰባው መልስ ባሪ በተባለ ሆቴል እያሉ ነበር በቁጥጥር ስር የዋሉት።

አንድ በፈረንሳይ የሚገኝ ተሰሚነት ያለው ሚድያ እንደገለፀው አህመድ አህመድን በሙስና የጠየቀው በፀረ ሙስና የሚሰራ (OCLIF) የተባለ ተቋም ሲሆን ፕሬዝዳንቱ ያስጠየቀው ጉዳይም ከጀርመኑ የትጥቅ አምራች ፑማ ጋር የፈፀሙት ውል ነው ብሏል።

ውሉን ለማዋዋል የማይገባቸው 739 ሺህ ዪሮ ተቀብለዋል ተብለው የተጠረጠሩት ፕሬዝዳንቱ በፓሪስ ከመታሰራቸው ውጭ እስካሁም ይፋዊ ዝርዝር ሃሳብ አልተሰጠም።

በቀጣት ቀናት በዋይዳድ ካዛብላንካ እና ኤስፔራንስ ደ ቱኒዝ ጉዳይ ከዋይዳድ ጋር በካስ ፍርድ ቤት ይፋጠጣል እየተባለ ያለው ካፍ ከወዲሁ በብዙ ብልሹ አሰራሮች ጋር እየተጠረጠረ ይገኛል።

የኤስፔራንስ ተቃውሞ

በካፍ ቻምፒየንስ ሊግ ያሸነፉት ዋንጫ እና ሜዳልያ እንዲመልሱ የታዘዙት ኤስፔራንሶች የካፍን ውሳኔ በፅኑ በመቃወም ጉዳዩን ወደ ካስ እንደሚወስዱት ገለፁ።

ክለቡ በይፋዊ የትዊተር ገፁ እንደገለፀው ከሆነ በቀጣይ ቀናት አስቸኳይ ስብሰባ አድርጎ የተወሰነለት ውሳኔ ለማስቀየር እና መብቱን ለማስከበር ካፍን በአለማቀፍ የስፖርት ገላጋይ ፍርድ ቤት ለመገተር እንደተዘጋጀ ገልፀዋል።

የፍፃሜው ጨዋታ ከአፍሪካ ዋንጫ በኃላ በደቡብ አፍሪካ ለማድረግ የወሰነው ካፍ ጨዋታው በአውሮፓውያን ዳኞች እንዲመራም ውሳኔ አስተላልፏል።

የቱኒዚያ ጠቅላይ ሚኒስቴር ተቃውሞ

የቻምፒዮንስ ሊግ ፍፃሜ ጨዋታ በገለልተኛ ሜዳ ላይ እንዲደገም መወሰኑ ያልተዋጠላቸው የቱኒዝያው ጠቅላይ ሚኒስትር ዮሱፍ ቻማድ ውሳኔውን በመቃወም በቱኒዝያ ድህንነት ጥርጣሬ ገብቷቸው ጨዋታውን ገለልተኛ ሜዳ እንዲደረግ የወሰኑትን ወርፈዋል። ” የድህንነት ኃይላችን በዓለም እንደ አብነት የሚጠቀስ ነው” ብለዋል። የክለቡ ደጋፊዎም ውሳኔው በተወሰነበት የፈረንሳው ዋና ከተማ ፓሪስ ሰልፍ ማድረጋቸው ተገልጿል።

የኢትዮጵያ ጥያቄ

የኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ካፍ በሞሮኮ ሮያል እግርኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዝዳንት ፋውዚ ሌካ ላይ የዲሲፕሊን እርምጃ እንዲወስድ ጠይቋል። ፕሬዝዳንቱ ከሳምንት በፊት በተካሄደው የካፍ ኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ፍፃሜ ላይ የእለቱ ዳኛ በዓምላክ ተሰማ ላይ ጥቃት አድርሰዋል በሚል ነው። በዛማሌክ እና ሬነሰንስ በርካኔ መካከል የተካሄደውን ጨዋታ ዛማሌክ በመለያ ምቶች አሸንፎ ዋንጫ ማንሳቱ የሚታወስ ነው።

የአፍሪካ ዋንጫ ዳኞች

ከሳምንታት በፊት በአፍሪካ ዋንጫ የሚዳኙ ዳኞችን የለየው ካፍ ስማቸውን ዛሬ ይፋ ሲያደርግ ኢትዮጵያዊያኑ በዓምላክ ተሰማ (ዋና) እና ተመስገን ሳሙኤል (ረዳት) ስማቸው ከተካተቱት መካከል ናቸው።

የሁለቱን ዳኞች መመረጥ በተመለከተ ከዚህ ቀደም በሶከር ኢትዮጵያ የተሰራ ዜና – LINK 

ሮበርት ኦዶንካራ

– የአዳማ ከተማው ግብ ጠባቂ ሮበርት ኦዶንካራ የዩጋንዳ ዝግጅትን ዘግይቶ ተቀላቅሏል። ከሴባስቲያን ድሳብር የ27 ተጫዋቾች ስብስብ ውስጥ የተካተተው ኦዶንካራ ከቀናት በፊት ወደ አቡ ዳቢ ለዝግጅት ያመራውን ቡድን በትላንትኔው ዕለት ነው የተቀላቀለው።