ጅማ አባጅፋር ላይ የእገዳ ውሳኔ ተላለፈ

ከይስሃቅ መኩርያ ጋር በክርክር የቆዩት ጅማ አባጅፋሮች ከፌደሬሽኑ አገልግሎት እንዳያገኙ ታግደዋል።

ከሶስት ወራት በፊት ይስሃቅ መኩርያ ጅማ አባጅፋር ከክለቡ ጋር ውል እያለኝ አለአግባብ አሰናብቶኛል ብሎ ክለቡ ላይ ክስ ማቅረቡ ይታወቃል። የተጫዋቹን ጥያቄ የተመለከቱት የፌደሬሽን የፍትህ አካላትም የተጫዋቹን ጥያቄ ተገቢነት አለው በማለት ክለቡ ለተጫዋቹ የሚገባውን ክፍያ እንዲከፈለው መወሰናቸው ይታወሳል። ሆኖም ክለቡ የፍትህ አካላትን ውሳኔ ባለመቀበል ጉዳዩ ወደ ዓለም አቀፍ ስፖርት ገላጋይ ፍርድ ቤት ( Cas) ቢወስደውም የፍትህ አካሉ የካስ ፍርድ ሂደት በተያዘለት ጊዜ መጠናቀቅ ባለመቻሉ ተጫዋቹ እየተጉላላ መሆኑ በደብዳቤው ላይ ገልጿል።

የተጫዋቹን አቤቱታ የተመለከተው የዲሲፕሊን ኮሚቴውም ክለቡ የፍትህ አካል ውሳኔን ተግባራዊ አለማድረጉን በመግለፅ ተግባራዊ እስኪያደርጉ ድረስ ክለቡን ከፌዴሬሽኑ አገልግሎት ማገዱን በደብዳቤ ገልጿል።


© ሶከር ኢትዮጵያ