በ15ኛ ሳምንት ሲቢኢ የኢትዮጵያ ፕሪሚየር ሊግ አዳማ ላይ በተደረጉ የመጨረሻ ቀን ጨዋታዎች ሀዋሳ ከተማ እና አዳማ ከተማ በጭማሪ ደቂቃዎች ባስቆጠሩት ግብ ከተጋጣሚዎቻቸው ነጥብ ተጋርተዋል።

ኢትዮጵያ ቡና ከ ሀዋሳ ከተማ
ጨዋታው በጅማሮው በሁለቱም ቡድኖች ጥሩ በሆነ እንቅስቃሴ የታጀበ ሲሆን በኳስ ቁጥጥር ረገድ ተመሳሳይ የሆነ ፉክክር ያስመለከተን ነበር። በሁለቱም ቡድኖች የግብ ክልል ላይ በፍጥነት መድረስ የቻሉ ሲሆን የመጀመሪያውን ሙከራ በማድረግ ረገድ ቡናማዎቹ ቀዳሚ ሲሆኑ በሻባን ሙሐመድ አማካኝነት ለግብ የቀረበ ሙከራ ሲያደርጉ ሀዋሳዎችም በበኩላቸው በሽመልስ በቀለ እና አብነት ደምሴ አማካኝነት ሙከራዎችን ማድረግ ችለዋል።

38ኛው ደቂቃ ላይ ኢትዮጵያ ቡናዎች ቀዳሚ መሆን የቻሉበትን ግብ አስቆጥረዋል። ዲቫይን ዋቹኩዋ ከመሀል ሜዳ ይዞት የገባው እና በጥሩ አንድ ሁለት ቅብብል የተጫወቱትን ኳስ በመጨረሻም ናትናኤል ፍሬው አቀብሎት ራሱ ዲቫይን ዋቹኩዋ ወደ ግብነት ቀይሮ ቡድኑን መሪ በማድረግ ወደ መልበሻ ክፍል አምርተዋል።
ከዕረፍት መልስ ቡናማዎቹ ድንቅ እና አዝናኝ በሆነ የእግር ኳስ ጨዋታ የተመለሱ ሲሆን ሲሆን 75ኛው ደቂቃ ላይ ናትናኤል ፍሬው እና አቡበከር አዳሙ በጥሩ ቅብብሎሽ ወደ ግብ በመድረስ ያገኙትን ዕድል አቡበከር አዳሙ ወደ ግብ ቢመታውም ግብ ጠባቂው ሰይድ ሀብታሙ መልሶታል። ጨዋታው መገባደጃ ደቂቃ ላይ ለቡናዎቹ ተጨማሪ የግብ ዕድልን ተቀይሮ በገባው አማኑኤል አድማሱ አማካኝነት ያገኙትን አጋጣሚ ለጥቂት በግብ ቋሚ ወደ ውጪ ወጥቷል።

መደበኛው የጨዋታ ሰዓት ተጠናቆ በተሰጠው ጭማሪ ደቂቃ (90+3) ላይ መነሻውን ከእጅ ውርወራ ያደረገው እና በተባረክ ሄፋሞ በግንባር ተገጭቶ የደረሰውን ኳስ የኢትዮጵያ ቡና ተከላካዮች መዘናጋትን ተከትሎ ጌታነህ ከበደ ወደ ግብነት በመቀየር የማታ ማታ ቡድኑ ነጥብ ተጋርቶ እንዲወጣ አስችሏል።
አዳማ ከተማ ከ ሲዳማ ቡና
በተጠባቂው ጨዋታ የመጀመሪያውን ግብ ለማስቆጠር አስራ ስድስት ደቂቃዎች ብቻ በቂ ነበሩ። 16ኛው ደቂቃ ላይ ከማእዘን ምት የተሻገረውን ኳስ በብርሃኑ በቀለ በግንባር ተጨርፎ የደረሰው መስፍን ታፈሰ አጨራረሱን በማሳመር ሲዳማ ቡናን መሪ ማድረግ ችሏል።

ብዙ ሙከራዎችን ባላስመለከተን አጋማሽ መደበኛው የጨዋታ ሰዓት መጠናቀቂያ ደቂቃ ላይ ከሜዳው የግራ መስመር ወደ መሀል ገብቶ በጥሩ የመጀመሪያ ንክኪ ያቀበለውን ኳስ መስፍን ታፈሰ በግራ እግሩ አክርሮ በመምታት ለራሱ እና ለክለቡ ሁለተኛውን ግብ አስቆጥሯል።
ከዕረፍት መልስ አዳማ ከተማዎች ቅያሪዎችን በማድረግ ወደ ሜዳ የተመለሱ ሲሆን 55ኛው ደቂቃ ላይ የሲዳማ ቡና ተጫዋቾች በአግባቡ ያላራቁትን ኳስ አቡበከር ሣኒ ወደ ግብነት በመቀየር አዳማ ከተማን ወደ ጨዋታው መልሷል።

ጨዋታው ሊጠናቀቅ በተሰጠው ጭማሪ ደቂቃ ላይ ድራማዊ ክስተቶችን ያስመለከተን ሲሆን 90+1 ላይ ከማእዘን ምት የተሻማውን ኳስ ሙጅብ ቃሲም በጥሩ አጨራረስ ወደ ግብነት በመቀየር አዳማ ከተማን ከሽንፈት መታደግ ችሏል። ጨዋታው ሊጠናቀቅ የዳኛ ፊሽካ ሲጠበቅ ቢኒያም ዐይተን ከአዳማ እንዲሁም የሲዳማው ብርሃኑ በቀለ የሞከሩት ኳስ የግቡን ቋሚ እና አግዳሚ ገጭቶ እንዲሁም በግብ ጠባቂው ናትናኤል ተፈራ ድንቅ ብቃት ወጥቶባቸዋል። ይህንንም ተከትሎ ጨዋታው 2-2 በሆነ ውጤት ተጠናቋል::

