አለማየሁ አባይነህ – ሲዳማ ቡና
ስለ ጨዋታው
“ጨዋታውን የመጀመሪያ አጋማሽ ላይ ጨርሰን መውጣት ይገባን ነበር፡፡ በመጀመሪያው አጋማሽ የተሻልን ነበርን ፤ በርካታ ግቦችን ማስቆጠር ይገባን ነበር፡፡ ነገር ግን ያንን ማድረግ አልቻልንም፡፡ በሁለተኛው አጋማሽ ልጆቼ ተቀዛቅዘው ነበር ፤ በመልሶ ማጥቃት ነበር ለመጫወት ያሰብነው፡፡ ነገርግን ጥቂት እድሎችን ነበር መፍጠር የቻልነው፡፡ በሁለተኛው አጋማሽ ከመስመር በሚነሱ ኳሶች ለመጠቀም ያደረጉት ጥረት የተሻለ አድርጓቸዋል፡፡”
በጨዋታው ስለነበራቸው አቀራረብ
“ከሜዳ ውጪ የነበረን ሪከርድ እና ውጤት ጥሩ አልነበረም ፤ የአዲስ አበባ መጫወቻ ሜዳ ምቹ ስለሆነ የማጥቃት አጨዋወትን ይዘን ቀርበናል፡፡ በተለይም በመጀመሪያው አጋማሽ አጥቅተን ብንጫወትም በርካታ እድሎችን አምክነናል፡፡ ነገርግን አጥቅተን ተጫውተን ለማሸነፍ ነበር ወደ ሜዳ የገባነው ይህንንም አሳክተናል፡፡”
ስዩም ከበደ – አዲስ አበባ ከተማ
ስለ ጨዋታው
“የዛሬው ጨዋታ ባብነው መልኩ አልሄደልንም ፤ ይህንንም ስንል በተለይ በመጀመሪያው አጋማሽ ሲዳማ ቡናዎች በብዙ መልኩ ከኛ የተሻሉ ነበሩ፡፡ ነገርግን በሁለተኛው አጋማሽ እኛ የተሻልን ነበርን፡፡ የተወሰኑ ለውጦችን አድርገን አቻ ለመውጣት ጥረት አድርገናል ነገርግን አልተሳካም፡፡”
ስለቀጣይ እቅድ
“አሁንም ዝም ብለን ቁጭ አላልንም ምናልባት በሁለተኛው ዙር ላይ አንዳንድ በሚጎድሉን ቦታዎች ላይ የተሻለ ነገር ለማድረግ 6 ተጫዋቾችን ከጋና እና ካሜሮን አስመጥተናል በዚህም ያሉብንን ክፍተቶች የሚደፍኑልን ከሆነ በቀጣዮ ዙር የአቅማችንን ጥግ ለመስጠት እንሰራለን፡፡”