የኢትዮጵያ ከ20 ዓመት በታች ሴቶች ብሔራዊ ቡድን ወደ ሀገር ቤት ተመልሰዋል

በፓናማ እና ኮስታሪካ አስተናጋጅነት ለሚካሄደው የሴቶች ከ20 ዓመት በታች የዓለም ዋንጫ ቅድመ ማጣርያ የመጀመርያ ጨዋታቸውን ከቡሩንዲ ጋር ቅዳሜ ዕለት አድርገው በሰፊ የግብ ልዩነት ያሸነፉት ተተኪዎቹ ሉሲዎች ወደ ሀገር ቤት ተመልሰዋል።

በአሰልጣኝ ፍሬው ኃይለገብርኤል እና ህይወት አረፋይኔ እየተመራ ቡሩንዲ ኢኒዋሪ ስታዲየም ላይ 5-0 በማሸነፍ የቅድመ መጣሪያውን የመጀመሪያ ጨዋታ በድል የጀመረው ቡድኑ በኢትዮጽያን ሰዓት አቆጣጠር ማምሻውን 3:30 አዲስ አበባ የደረሰ ሲሆን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ አባል አብዱራዛቅ መሐመድ እንዲሁም የእግር ኳስ ልማት ምክትል ሰብሳቢ አቶ ሰለሞን ገብረሥላሴ በስፍራው በመገኘት ለልዑካን ቡድኑ አቀባበል አድርገዋል። የእንኳን ደህና መጣቹ መልዕክት ከተላለፈ በኋላም ወደተዘጋጀላቸው ማረፊያ (ኢትዮጵያ ሆቴል) በቀጥታ አምርተዋል።

ከ20 ዓመት በታች የሴቶች ብሔራዊ ቡድን ከቡሩንዲ ጋር የሚያደርገው የመልስ ጨዋታን ጥር 24 የሚያከናውን ሲሆን ባህር ዳር ስታዲየም ጨዋታው የሚከናወንበት ቦታ ነው።


© ሶከር ኢትዮጵያ