የወልቂጤ ም/ፕሬዝዳንት እና የቦርድ ፀኃፊ ራሳቸውን ከኃላፊነት ማንሳታቸውን አስታወቁ

የወልቂጤ ከተማ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ አበባው ሰለሞን እና የክለቡ ቦርድ ፀኃፊ የሆኑት ጌቱ ደጉ (ረ/ፕ/ር) ራሳቸውን ከሥራ ማግለላቸውን አስታውቀዋል።

በ14ኛ ሳምንት የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ወልቂጤ ከተማ በሜዳው በሲዳማ ቡና 1-0 በተሸነፈበት ጨዋታ ላይ የወልቂጤ ደጋፊዎች በአመራሩ ላይ ጠንከር ያለ ተቃውሞ የገለፁ ሲሆን ይህን መነሻ ያደረጉ እና በሌሎች የክለቡ ውስጥ ጉዳዮች ዙርያ ያላቸውን ቅሬታ በመግለፅ ራሳቸውን ከክለቡ ሥራ እንዳገለሉ በጨዋታው ዕለት ምሽት ላይ ሶከር ኢትዮጵያ ማረጋገጫ አግኝታለች። አሁን ደግሞ ሁለቱ አመራሮች ራሳቸውን ማግለላቸውን የሚገልፅ ደብዳቤ ለክለቡ ማስገባታቸውን ለማወቅ ችለናል።

አቶ አበባው ሰለሞን (ፎቶ) ወልቂጤ ከተማ ጋር ከታችኛው ሊግ ጀምሮ ለበርካታ ዓመታት ክለቡን ያገለገለ ሲሆን ክለቡ ወደ ፕሪምየር ሊግ እንዲያድግ ከፍተኛውን ሚና እንደተወጣ ይነገርለታል።

ከውሳኔው ጋር በተያያዘ ያሉን ቀጣይ ሁኔታዎች ተከታትለን የምንዘግብ ይሆናል።

© ሶከር ኢትዮጵያ