አሰልጣኝ ውበቱ አባተ በተጫዋቾች ጉዳት ዙርያ ማብራርያ ሰጥተዋል

የዋልያዎቹ አሰልጣኝ ውበቱ አባተ በብሔራዊ ቡድኑ ተጫዋቾች የጉዳት እና ተያያዥ ጉዳዮች ዙርያ ማብራርያ ሰጥተዋል።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድንን በተመለከተ በፌዴሬሽኑ ፅህፈት ቤት አሁን እየተሰጠ በሚገኘው መግለጫ አሰልጣኝ ውበቱ አባተ እንዳስታወቁት በስብስባቸው ከሚገኙ ሃያ ስድስት ተጫዋቾች መካከል ሱራፌል ዳኛቸው፣ አቡበከር ናስር፣ ሙጂብ ቃሲም እና አማኑኤል ዮሐንስ ጉዳት ማስተናገዳቸውን ገልጸው የግሮን ጉዳት የገጠመው አማኑኤል እና ጡንቻ መሳሳብ ጉዳት ያስተናገደው አቡበከር አገግመው ወደ ልምምድ ሲመለሱ የጉልበት ግጭት ያስተናገደው ሱራፌል ጉዳቱ ቀለል ያለ እንደሆነ እና የሙጂብ ግን ጠንከር ያለ የታፋ ጉዳት መሆኑን አስታውቀዋል።

አሰልጣኝ ውበቱ በተጨማሪነት አሁን በስብስቡ ከሚገኙ ተጫዋቾች የሚቀነስ ተጫዋች የማይኖር ሲሆን 23 ተጫዋቾች ወደ ኒጀር ሲጓዙ ቀሪዎቹ ሦስቱ ደግሞ በአዲስ አበባ ቆይተው ቡድኑ ሲመለስ ለባህር ዳሩ ጨዋታ ይቀላቀላሉ ብለዋል።

© ሶከር ኢትዮጵያ


👉ሳንዘናጋ አስፈላጊውን ጥንቃቄ በማድረግ ራሳችንን ከኮሮና ቫይረስ እንጠብቅ!