ሰበታ ከተማ አዲስ ምክትል አሠልጣኝ አግኝቷል

አሠልጣኝ ዘላለም ሽፈራውን ዋና አሠልጣኝ አድርጎ የሾመው ሰበታ ከተማ አዲስ ምክትል አሠልጣኝ መሾሙ ታውቋል።

በተጠናቀቀው የውድድር ዘመን 37 ነጥቦችን በመሰብሰብ 5ኛ ደረጃን ይዞ ያጠናቀቀው ሰበታ ከተማ ከሳምንታት በፊት ዘላለም ሽፈራውን ዋና አሠልጣኝ አድርጎ መሾሙ ይታወቃል። አሠልጣኙ መንበሩን ከያዙ በኋላም በዝውውር ገበያው ላይ በመሳተፍ የተለያዩ ተጫዋቾችን ሲያስፈርሙ ቆይተዋል።

ሶከር ኢትዮጵያ አሁን ያገኘችው መረጃ ደግሞ ክለቡ አዲስ ምክትል አሠልጣኝ ማምጣቱን ይጠቁማል። የአሠልጣኝ ዘላለም ምክትል የሆኑት ዳንኤል ገብረማርያም (ኢንስትራክተር) ናቸው። ከዚህ ቀደም በኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን የቴክኒክ ኃላፊ የነበሩት እና ወደ አዲስ አበባ ከተማ፣ አዳማ ከተማ እና ኢትዮጵያ መድን አምርተው በተመሳሳይ ሙያ አገልግለው የነበረው አሠልጣኝ ዳንኤል በተጠናቀቀው ዓመት በኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ የሚሳተፈውን ክለብ ኢኮሥኮን እያሰለጠኑ እንዳሳለፉ ይታወሳል።