ድሬዳዋ ከተማ የዛሬውን ጨዋታ መነሻ በማድረግ ቅሬታውን አቅርቧል

በ28ኛው ሳምንት ከባህር ዳር ከተማ ጋር ቀትር ላይ የተጫወተው ድሬዳዋ ከተማ ለሊጉ የበላይ አካል የቅሬታ ደብዳቤ አስገብቷል።

በባህር ዳር ስታዲየም ዛሬ ቀትር ባህር ዳር ከተማ ከድሬዳዋ ከተማ ያደረጉት ጨዋታ በባህር ዳር ከተማ 1-0 አሸናፊነት መጠናቀቁ ይታወሳል። ከጨዋታው መካሄድ አስቀድሞ እና መጠናቀቅ በኋላ ድሬዳዋ ከተማዎች ‘ዳኝነቱ ላይ ቅሬታ አለብን’ በማለት ለኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ አክስዮን ማኅበር ሁለት ደብዳቤ አስገብተዋል።

ድሬዳዋ መረጃ ደረሰኝ ብሎ ከጨዋታው በፊት በፃፈው ደብዳቤ “ባህር ዳር ከተማ ቡድን ከዳኞች ጋር ግኑኝነት ፈጥረዋል የሚል መረጃ ስለደረሰን እንደ ክለባችን አቋም በችሎታ ተጫውቶ ማሸነፍ እንጂ በዚህ መልኩ እንዳይሆን ፍላጎት የሌለን ስለሆነ የሊጉ አክስዮን ማኅበር ጉዳዮን በአፅኖት ተከታትሎ አስፈላጊውን ክትትል በማድረግ ለዳኞች ኮሚቴና ለአወዳዳሪው አካል አስፈላጊውን መመርያ እንዲሰጥልን እንጠይቃለን።” የሚል ሀሳን አስቀምጧል።

ከጨዋታው መጠናቀቅ በኋላ ደግሞ “በ28ኛ ሳምንት ከባህርዳር ከተማ ጋር ከመጫወታችን በፊት በደረሰን መረጃ የዳኝነት ስጋት እንዳለብን በደብዳቤ ገልፀን ነበር። በመሆኑም በጨዋታው 89ኛው ደቂቃ ግልፅ ጎል አስቆጥረን እጅግ ውድ ነጥብ ልናገኝ በተቃረብንበት ሰዓት ፌደራል ዳኛ ተፈሪ አለባቸው ምንነቱ ባልታወቀ ምክንያት ጎሉን ሽሮ ቡድናችን ላይ ትልቅ ጉዳት አድርሷል። ስለሆነም አክስዮን ማኅበሩ የጨዋታውን ምስል በማየት ቡድናችን ላይ የደረሰውን ውጤት የሚያካክስ ወሳኝ እርምጃ እንዲወስድ እንጠይቃለን።” ካለ በኋላ “ከዚሁ ጋር ተያይዞ ግብጠባቂው ፍሬው ባቀረበው የመብት ጥያቄ የተመለከተው ቢጫ እንዲነሳልን እንጠይቃለን የሚል ደብዳቤ ማስገባታቸውን አውቀናል።