ሴቶች ፕሪምየር ሊግ | ቦሌ ክ/ከተማ መሪነቱን አጠናክሯል

የኢትዮጵያ ሴቶች ፕርሚየር ሊግ የሰባተኛ ሳምንት ጨዋታዎች ላይ የሰዓት እና የቀን ሽግሽግ ተደርጎ በዛሬው ዕለት አንድ ጨዋታ ተከናውኗል።

ቀን ስምንት ሰዓት ላይ የሊጉ መሪ ቦሌ ክ/ከተማ ከአዲስ አበባ ከተማ ጋር ተገናኝቶ ከሰፊ ግብ ልዩነት ጋር ተጋጣሚውን ማሸነፍ ችሏል። በመጀመሪያ አጋማሽ ሁለቱም ቡድኖች በኳስ ቁጥጥር ተመጣጣኝ የሚባል ጥሩ ፉክክር አስመልክተዋል ፤ እንዲሁም ሁለቱም በተደጋጋሚ የእርስ በርስ ግብ ለመድፈር የሚያድርጉት እንቅስቃሴ ለጥቂት ሳይሳካላቸው ሲቀር ለመመልከት ትችሏል። ቦሌዎች ከተጋጣሚያቸው የተሻለ የግብ ሙከራ ማድረግ ችለዋል። ሆኖም ግን በአንደኛው አጋማሽ ግብ ሳይቆጠር ወደመልበሻ ክፍል ለመመለስ ተገደዋል።


በሁለተኛው አጋማሽ የተሻል አጨዋወት ይዘው የገቡት ቦሌዎች ሁለተኛ አጋማሽ እንደተጀመር ግብ ለማስቆጠር ኳስን ይዘው ተቃራኒ ቡድን ላይ ጫና ፈጥረው ሲጫውቱ ተስተውለዋል። ከብዙ የግብ ሙከራዎች በኋላ በ50ኛው ደቂቃ አማካዩዋ ሚልዮን ጋይም በግሩም ሁኔታ ከርቀት ሆና የመታችው ኳስ ወደግብነት ተቀይሮ ቦሌ መሪ እንዲሆን አድርጋለች።

አዲስ አበበ ከተማ በአንፃሩ ግብ ከተቆጠረባቸው በኋላ የአቻነት ግብ ለማስቆጠር ሙከራ ቢያድርጉም ጥሩ ሆነው የዋሉት የቦሌዎቹን ተከላካይ መስመር አልፈው ግብ ማስቆጠር ተስኗቸዋል። ቦሌዎቹም እንዲሁ ተጨማሪ ግብ ለማስቆጠር በመልሶ ማጥቃት ኳስን ይዘው ወደፊት ገፍተው ተጫውተዋል። በ78ኛው ደቂቃ የፊት መስመር ተጫዋች የሆነችው ትዕግሥት ወርቄ ኳስን ይዛ ወደ ግብ ክልል በምትገባበት ወቅት የአዲስ አበባ ከተማ ተከላካዮች በሰሩት ጥፋት ፍፁም ቅጣት ምት አግንተው ፍቅርአዲስ ገዛኸኝ አስቆጥራ ግቡን ወደሁለት በማሳደግ መሪነታቸውን አጠናክራለች።

ቦሌ ክ/ከተማ እስከመጨረሻዎቹ ደቂቃዎች ተጨማሪ ግብ ለማስቆጠር በኳስ ቁጥጥር በልጠው የግብ ሙከራዎችን ሲያደርጉ ተስተውለዋል። በ88ኛው ደቂቃ ዛሬ ለቦሌዎች ጥሩ እንቅሰቃሴ ሲታደርግ የዋለችው ትዕግሥት ወርቄ ከተከላካይ ጀርባ የተጣለውን ኳስ ከግብ ጠባቂ ጋር ተገናኝታ ግብ ጠባቂዋን አታላ በማለፍ ግሩም ግብ አስቆጥራ ቦሌ ክ/ከተማ በሰፊ ግብ ልዩነት አሸንፎ መሪነታቸውን እንዲያጠናክሩ አድርጋለች።

የሰባተኛ ሳምንት መርሃግብሮች የቀን እና የሰዓት ሽግሽግ ተደርጎባቸው ነገ እና ከነገ ወዲያ የሚደረጉ ሲሆን፦

ነገ ረቡዕ ጠዋት 4:00
ይርጋጨፌ ቡና ከ መቻል

ከሰዓት 8:00
ሀምበርቾ ከ ልደታ ክ/ከተማ

10:00
ኢትዮ ኤሌክትሪክ ከ አዳማ ከተማ

ከነገ ወዲያ ሀሙስ

ጠዋት 4:00
ሀዋሳ ከተማ ከ ድሬዳዋ

ከሰዓት 8:00
ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ከ ቅዱስ ጊዮርጊስ

10:00
ሲዳማ ቡና ከ አርባምንጭ ከተማ