​አፍሪካ | ሚቾ ከዩጋንዳ ብሔራዊ ቡድን ጋር ተለያይተዋል

የቀድሞው የቅዱስ ጊዮርጊስ አሰልጣኝ ሰርዮቪች ሚሉቲን “ሚቾ” በይፋ ከዩጋንዳ እግርኳስ ፌዴሬሽኖች ማህበር (ፉፋ) ጋር የነበራቸውን ውል በማቋረጥ ተለያይተዋል፡፡

ሚቾ በብሔራዊ ቡድኑ አሰልጣኝነታቸው ያለፉትን 6 ወራት ካለደሞዝ ሲሰሩ እንደቆዩ በመግለፅ ከ64ሺህ ዶላር በላይ ውዝፍ ደሞዝ ካልተከፈላቸው በስራቸው እንደማይቀጥሉ ለሶከር ኢትዮጵያ አስተያየታቸውን ሰጥተው ነበር፡፡ “ካለ ደሞዝ ኮንትራቱ ዋጋ አይኖረውም፡፡ ስለዚህ ወደምፈልግበት እንድጓዝ እድሉን ሊሰጡኝ ይገባል” ብለዋል፡፡

በዚህ ሳምንት በወኪላቸው ኢቫን ስታንኮቪች በኩል ከፌዴሬሽኑ ጋር ሲወያዩ የቆዩት ሚቾ ድርድሩ ካለ ውጤት መጠናቀቁን ተከትሎ ውላቸውን በስምምነት አቋርጠዋል፡፡

በ2 አጋጣሚዎች (1997-98 እና 2000-2002) ቅዱስ ጊዮርጊስን የመሩት ሰርዮቪች ሚሉቲን ከክሬንስ ጋር መለያየታቸውን ተከትሎ ከተለያዩ የአፍሪካ ክለቦች በተለይም ከኦርላንዶ ፓያሬትስ እና ዛማሌክ ጋር ስማቸው እየተያያዘ ይገኛል፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *