የኢትዮጵያ ከፍተኛ ሊግ የሳምንቱ ውሎ

በአምሀ ተስፋዬ እና ቴዎድሮስ ታደሰ


የምድብ ሀ ጨዋታዎች ተጠናቀዋል

የከፍተኛ ሊጉ ምድብ ሀ ጨዋታዎች ከምድብ ለ በአንድ ሳምንት ቀድመው ተጠናቀዋል። እሁድ እና ሰኞ በተደረጉ ጨዋታዎችም የወረዱ ሶስት ቡድኖች ሲታወቁ ለውዝግብ በር የከፈተ ክስተትም ተከስቷል።

ደሴ ከተማ ከወሎ ኮምበልቻ ባደረጉት ጨዋታ ደሴ ከተማ 2-0 አሸንፎ በመጨረሻው ሳምንት ከወራጅ ቀጠናው መውጣት ችሏል። በተመሳሳይ ሰዓት በተደረገው የፌዴራል ፖሊስ እና ሽረ እንዳሥላሴ ጨዋታ ደግሞ በሽረ 3-1 አሸናፊነት ተጠናቋል። በጨዋታው መጀመርያ ፌዴራል ፖሊሶች በሁለት የሽረ ተጫዋቾች ላይ የተገቢነት ክስ ያስመዘገቡ በመሆናቸው ጉዳያቸው የሚታይ ሲሆን ክሱ ተቀባይነት ካገኘ ፌዴራል በፎርፌ አሸናፊ ሆኖ ሲተርፍ ደሴ ከተማ በምትኩ የሚወርድ ይሆናል። ተቀባይነት ካላገኘ ደግሞ ደሴ መትረፉ ይረጋገጣል። በሌላ የሰኞ ጨዋታ ቡራዩ ላይ የካ ክፍለ ከተማ ኢኮስኮን 2-0 በማሸነፍ አለመውረዱን መመረጋገጥ ችሏል።

ከዚህ ቀደም አክሱም ከተማ በሰበታ ከተማ 1-0 በተሸነፈበት ጨዋታ አክሱሞች ያስመዘገቡት የተጫዋች ተገቢነት ክስ ተቀባይነት አግኝቶ አክሱም ከተማ በፎርፌ አሸናፊ እንዲሆን ተወስኗል።

የምድብ ጨዋታዎች መጠናቀቃቸውን ተከትሎ አስቀድሞ ወደ ፕሪምየር ሊግ ማደጉን ያረጋገጠው ባህርዳር ከተማ በቀዳሚነት ሲያጠናቅቅ ሽረ እንዳሥላሴ 2ኛ ደረጃን ይዞ በማጠናቀቅ የምድብ ለ ሁለተኛ ጋር ለመለያ ጨዋታ ዝግጁ ሆኖ እየጠበቀ ይገኛል።

የ30ኛ ሳምንት ውጤቶች 


ሰኞ ነሀሴ 14 ቀን 2010

ደሴ ከተማ 2-0 ወሎ ኮምቦልቻ

ፌዴራል ፖሊስ 1-3 ሽረ እንዳስላሴ

የካ ክ/ከተማ 2-0 ኢኮስኮ


እሁድ ነሀሴ 13 ቀን 2010

አውስኮድ 2-0 ኢትዮጵያ መድን

ሱሉልታ ከተማ 1-2 ሰበታ ከተማ

ባህር ዳር ከተማ 2-0 አአ ከተማ

ነቀምት ከተማ 3-0 አክሱም ከተማ (ፎርፌ)


ረቡዕ ነሀሴ 9 ቀን 2010

ቡራዩ ከተማ 1-1 ለገጣፎ- ለገዳዲ


የደረጃ ሰንጠረዥ

የምድብ ለ  ትንቅንቅ ቀጥሏል

በምድብ ለ ወደ ፕሪምየር ሊግ የመግባት እድል ያላቸው ሶስት ክለቦች ሰኞ በተመሳሳይ 04:00 ላይ ባደረጉት ጨዋታ በማሸነፋቸው አንደኛ እና ሁለተኛ ደረጃ ይዘው የሚያጠናቅቁ ክለቦችን ለመለየት የ30ኛው ሳምንት ጨዋታዎችን መጠበቅ የግድ ሆኗል።

በሁለት ነጥቦች ልዩነት ምድቡን የሚመራው ደቡብ ፖሊስ ወደ ዱራሜ አቅንቶ ሀምበሪቾን 3-2 በማሸነፍ ወደ ፕሪምየር ሊግ ለማደግ ከጫፍ ደርሷል። ገና በመጀመሪያው ደቂቃ ኤሪክ ሙራንዳ ግብ አስቆጥሮ ደቡብ ፖሊስን ቀዳሚ ማድረግ ሲችል በ7ኛው ደቂቃ ላይ ቴዲ ታደሰ ሀምበሪቾን አቻ አድርጓል። በ17ኛው ደቂቃ ላይ ዮናስ  ታዬ ግብ አስቆጥሮ ሀምበሪቾን ወደ መሪነት ቢያሸጋግርም መሪ ቢያደርግም በ25ኛው ደቂቃ በኃይሉ ወገኔ ደቡብ ፖሊስ ወደ አቻነት መልሶታል። ከጎሎቹ በኋላ ተጠማሪ ጎል ለመመልከት ረጅም ደቂቃዎች የፈጁ ሲሆን ፍፁም ደስይበለው በደቡ ፖሊስ ግብ ጠባቂ በተሰራበት ጥፋት ጉዳት አስተናግዶ ለረጅም ደቂቃዎች ጨዋታው ለመቋረጥ ተገዶ በደጋሚ ሲቀጥል በ85ኛው ደቂቃ ኤሪክ ሙራንዳ ለራሱ ሁለተኛ ለቡድኑ ሶስተኛ ጎል አስቆጥሮ ጨዋታወ በደቡብ ፖሊስ 3-2 አሸናፊነት መጠናቀቅ ችሏል።

ጅማ ላይ ሻሸመኔ ከተማን ያስተናገደው ጅማ አባ ቡና ሻሸመኔ ከተማን 5-1 ቢያሸንፍም ፕሪምየር ሊጉን በቀጥታ ለመቀላቀል የመጨረሻው ሳምንት ጨዋታ መጠበቅ የግድ ሆኖበታል። በመጀመርያ 5 ደቂቃዎች ጅማ አባቡናዎች በቴዎድሮስ ታደሰ እና በሀይደር ሸረፋ ለግብ የቀረቡ ሙከራዎች ቢያደርጉም በሻሸመኔ ግብ ጠባቂ በኃይሉ አባተ ጥረት ወደግብነት ሳይቀየሩ ቀርተዋል። በሒደት ሁለቱም ቡድኖች ተቀዛቅዘው በመሀል ሜዳ ላይ በሚደረጉ እቅስቃሴዎች ተገድበው ቢቆዩም በ17 ደቂቃ ዳዊት ተፈራ ባስቆጠራት ግብ ባለሜዳዎቹን ቀዳሚ ማድረግ ችሏል። ከግቧ መቆጠር በኋላ  መነቃቃት ያሳዩት አባ ቡናዎች ከ5 ደቂቃዎች በኃላ ሁለተኛውን ግብ በእለቱ መሀል ሜዳውን  በጥሩ ሁኔታ ሲመራ ከነበረው ሀይደር ሸረፋ የተገኘውን ኳስ ተመስገን ደረሰ ከሳጥን ውጭ በግሩም ሁኔታ ባስቆጠረው ጎል ማግኘት ችለዋል። በ30ኛው ደቂቃ አብርሃም ዓለሙ የሻሽመኔዎችን ተስፋ ያለመለመች ግብ ቢያስቆጥርም በ34ኛው ደቂቃ ሀይደር ሸረፋ ከርቀት ያስቆጠራት ግብ ሻሸመኔዎች ላይ የታየውን ተስፋ ያደበዘዘች ነበረች። የመጀመሪያው አጋማሽም በአባ ቡና 3-1 መሪነት ተጠናቋል።

ከእረፍት መልስ 48 ደቂቃ ብዙዓየሁ ከሻሸመኔ ግብጠባቂ በሀይሉ ጋር ተገናኝቶ የተመለሰውን ኳስ ቴዎድሮስ ታደሰ አስቆጥሮ መሪነቱን ወደ 4-1 ሲያሰፋ ከ10 ደቂቃዎች በኃላ 58ኛው ደቂቃ ላይ ሱራፌል ጌታቸው የማሳረጊያውን ጎል አስቆጥሯል። አባ ቡናዎች በተደጋጋሚ ከግብ ጠባቂ ጋር አንድ ለአንድ እየተገናኙ በኃይሉ አባተ ያዳናቸው እንዲሁም እርስ በእርስ ቅድሚያ ባለመሰጣጠት ባመከኗቸው አጋጣሚዎች ምክንያት ተጨማሪ ግቦችን መመልከት ሳይቻል ቀርቷል።

በጨዋታው 65ኛው ደቂቃ የባለሜዳዎቹ ደጋፊዎች ደስታቸውን ርችቶችን በማፈዳት በመግለፃቸው በተነሳ ውዝግበ ጨዋታው ለ10 ደቂቃዎች ተቋርጦ ሲቀጥል በጨዋታው መገባደጃ ላይ የአባ ቡና ደጋፊዎች የክለቡ አመራሮች ላይ ከባድ ተቋውሞ ያሰሙ ሲሆን የተጫዋቾቹን ደመወዝ እንዲከፈላቸው እንዲሁም የክለቡ ህልውና አጠያያቂ በመሆኑ ስጋታቸውን ገልፀዋል።

ሀላባ ላይ ሀላባ ከተማ ከ ቤንጅ ማጂ ቡና ጋር ያደረገው ጨዋታ በሀላባ 4-1 አሸናፊነት ቢጠናቀቅም በቀዳሚነትም ሆነ በሁለተኝነት ለማጠናቀቅ በሌሎቹ ቡድኖች ላይ የተመሰረተ እድል ለመያዝ ተገዷል። ጨዋታው በተጀመረ በ2ኛው ደቂቃ ተመስገን ይልማ ከመስመር በኩል ይዞት የገባውን ኳስ ሞክሮ ግብ ጠባቂው ባዳነበት ኳስ የግብ አጋጣሚ መፍጠር የጀመሩት ሀላባዎች በ4ኛው ደቂቃ ላይ በተመስገን ይልማ ላይ በተሰራ ጥፋት የተሰጠውን ፍፁም ቅጣት ምት ስንታየው መንግስቱ ወደ ግብነት በመለወጥ ቀዳሚ መሆን ችለዋል። በይበልጥ ተጭነው የተጫወቱት ሀላባዎች በ17ኛው ደቂቃ የስንታየው መንግስቱ ጎል ልዩነቱን አስፍተዋል። በጨዋታው በርካታ የግብ እድሎችን የፈጠሩት ሀላባ ከተማዎች ተጨማሪ ግብ ማስቆጠር የሚችሉበት እድል በመጀመሪያው አጋማሽ አባክነዋል። በተለይም በ28ኛው ደቂቃ ተመስገን ይልማ ከግብ ጠባቂው ጋር ተገናኝቶ የወጣበት እንዲሁም በ34ኛው ደቂቃ መሀመድ ናስር፣ በ42ኛው ደቂቃ ስንታየው መንግስቱ ያደረጓቸው ሙከራዎች ተጠቃሽ ነበሩ።

ከዕረፍት መልስ የመጀመሪያውን 15 ደቂቃ ተጭነው የተጫወቱት ቤንች ማጂ ቡናዎች በ47ኛው ደቂቃ ላይ ኤሪክ ኮልማን በግራ መስመር ያሻገረውን ኳስ ፉአድ መሐመድ ባስቆጠረው ጎለ ልዩነቱን ቢያጠቡም ብዙመ ሳይቆዩ የበላይነቱ በሀላባ ተወስዶባቸዋል። በ60ኛው ደቂቃ ወደ ሜዳ ተቀይሮ የገባው አስቻለው ኡታ የሀላባን ሶስተኛ ግብ አስቆጥሮ ልዩነቱን መልሶ ሲያሰፋ ከ80ኛው ደቂቃ ጀምሮ ከቤንች ማጂ ቡና መቀመጫ ጀርባ የነበሩት ደጋፊዎች ጋር እሰጣ ገባ የተጀመረ ሲሆን ምክንያቱ ደሞ የቤንች ማጂ ኮቺንግ ስታፍ ከጅማ አባ ቡናዎች የስልክ ልውውጥ እያደረጉ ነው በሚል ነበር። በሀላባ ደጋፊ ማህበር የስልክ ንግግሩን እንዲያቁም የተጠየቀው የቤንጅ ማጂ ቡና አባል ንትርኩን ከደጋፊዎች ጋር የቀጠለ ሲሆን በዚህ ሒደት በ89ኛው ደቂቃ ስንታየው መንግስቱ ሶስተኛ ጎሉን አስቆጥሮ ሐት-ትሪክ በመስራት ጨዋታው በሀላባ 4-1 አሸናፊነት ተጠናቋል። በጨዋታው የጀመረው ውዝግብ ግን እስከ ፍፃሜው ዘልቆ አላስፈላጊ ዛቻ እና የድንጋይ ውርወራዎች ታይተዋል። በስተመጨረሻም የሀላባ ደጋፊ ማኅበር የቤንጅን ማጂ ቡና ቡድንን በሀላባ ከተማ መኪና በመሸኘት ሁኔታው የተረጋጋ መልክ መያዝ ችሏል።
የምድቡ ጨዋታዎች ሊጠናቀቁ የአንድ ሳምንት እና የተስተካካይ ጨዋታዎች እድሜ ሲቀር አንደኛ እና ሁለተኛ ሆነው የሚጨርሱ ክለቦች እንዲሁም መቂ ከተማን ተከትለው የሚወርዱ ሁለት ክለቦች የሚለዩ ይሆናል።


የ29ኛ ሳምንት ውጤቶች 


የደረጃ ሰንጠረዥ


ሰኞ ነሀሴ 14 ቀን 2010

ጅማ አባ ቡና 5-1 ሻሸመኔ ከተማ

ሀምበሪቾ 2-3 ደቡብ ፖሊስ

ሀላባ ከተማ 4-1 ቤንች ማጂ ቡና


እሁድ ነሀሴ 13 ቀን 2010

ድሬዳዋ ፖሊስ 2-1 ወልቂጤ ከተማ

ካፋ ቡና 1-1 ዲላ ከተማ

ነጌሌ ከተማ 3-0* መቂ ከተማ (ፎርፌ)

ስልጤ ወራቤ 2-1 ቡታጅራ ከተማ

ናሽናል ሴሜንት 3-0 ሀዲያ ሆሳዕና

የደረጃ ሰንጠረዥ