የአፍሪካ ሴቶች ዋንጫ የምድብ ድልድል ይፋ ሆኗል

ለ11ኛ ጊዜ በጋና አስተናጋጅነት የሚከናወነው የአፍሪካ ሴቶች ዋንጫ ከኅዳር 8-22 በሁለት ከተሞች (አክራ እና ኬፕ ኮስት) ይከናወናል። 

ስምንት ሀገራትን የሚያሳትፈው ይህ ውድድር እሁድ ዕለት አክራ በሚገኘው በሞቬምፒክ አምባሳደር ሆቴል የምድብ ድልድሉ ሲከናወን በሚከተለው መልኩ ሆኗል። 

ምድብ ሀ – ጋና፣ ካሜሩን፣ ማሊ፣ አልጄርያ

ምድብ ለ – ናይጄርያ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ዛምቢያ፣ ኬንያ

ውድድሩ በ16 ዋና እና 16 -ረዳት ኢንተርናሽናል ዳኞች እንደሚመራ ካፍ ሲያሳውቅ ኢትዮጵያዊቷ ሊዲያ ታፈሰ በካፍ ከተመረጡት ዋና ዳኞች ዝርዝር ውስጥ ተካታለች። ሊዲያ በ2016 በካሜሩን የተስተናገደው 10ኛው የአፍሪካ ሴቶች ዋንጫ የመክፈቻ ጨዋታን መምራቷ የሚታወስ ነው። 

ናይጄርያ ስምንት ጊዜ፣ ኢኳቶርያል ጊኒ ደግሞ ቀሪዎቱን ሁለት ውድድሮች ባሸነፉበት የአፍሪካ ሴቶች ዋንጫ ላይ ኢኳቶርያል ጊኒ ለውድድሩ አልፋ የነበረ ቢሆንም በተጫዋች ተገቢነት ክስ ታግዳ በምትኳ ኬንያ ማለፏ ይታወቃል። በተመሳሳይ የተገቢነት ክስ በአልጄርያ ላይ አቅርባ የነበረችው ኢትዮጵያ ክሷ ውድቅ መደረጉም አይዘነጋም። 

ለሶስት ጊዜ በውድድሩ ላይ የተሳተፈችው ኢትዮጵያ ከ2012 የኢከኳቶርያል ጊኒ የአፍሪካ ሴቶች ዋንጫ በኋላ በተደረጉ ሶስት ውድድሮች ላይ ሳትሳተፍ ቀርታለች።