የይሁን እንደሻው ማረፊያ ዐፄዎቹ ሆነዋል

ፋሲል ከነማ የአማካይ ሥፍራ ተጫዋቹ ይሁን እንደሻውን አስፈርሟል።

በተቋረጠው የ2011 የውድድር ዓመት በሀዲያ ሆሳዕና በግሉ ጥሩ ጊዜ ያሳለፈው ይሁን የውል ዘመኑ መጠናቀቁን ተከትሎ ስሙ ከበርካታ ክለቦች ጋር ሲያያዝ ቢቆይም ዛሬ በተከፈተው የዝውውር መስኮት ወደ ፋሲል ከነማ በሁለት ዓመት ማምራቱ ተረጋግጧል።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን አማካይ የሆነው ይሁን በመተሐራ ስኳር የእግርኳስ ሕዮወቱን ጀምሮ በድሬዳዋ ከተማ ስኬታማ ጊዜ በማሳለፍ ቡድኑ ወደ ፕሪምየር ሊግ እንዲያድግ ረድቷል። በመቀጠልም በ2010 ወደ ጅማ አባ ጅፋር አምርቶ ቡድኑ የፕሪምየር ሊግ ዋንጫ ሲያነሳ ወሳኝ ሚና የተጫወተ ሲሆን በ2011 ወደ ሀዲያ ሆሳዕና አምርቶ ሲጫወት ቆይቷል።

“የዝውውር ቀኑን መከፈት ስጠብቅ ነበር። ምክንያቱም ህጋዊ ፊርማ እንዲኖረኝ ስለምፈልግ። ከመጀመሪያውም ትልቅ ክለብ መጫወትን አስቤ ስዘጋጅ ቆይቻለሁ። ይኸው ስመኘው ወደነበረው ትልቅ ክለብ የተሻለ ነገር ለመሥራት ስል ፈርሜያለሁ። ጥሩ ነገር አሳየቼ ከፋሲል ጋር ሁለተኛ የፕሪምየር ሊግ ዋንጫዬን አሳካለሁ።” ሲል ተጫዋቹ ከፊርማው በኃላ ለሶከር ኢትዮጵያ ተናግሯል፡፡

© ሶከር ኢትዮጵያ


👉እጅዎን በተደጋጋሚ በሳሙና በአግባቡ በመታጠብ አልያም አልኮል እና ሳኒታይዘር በመጠቀም

👉ከሰዎች ጋር ንክኪ በማስወገድ

👉ከአላስፈላጊ እንቅስቃሴ በመገደብ፣ አካላዊ ርቀት በመጠበቅ እና በቤት በመቆየት ራሳችንን ከኮሮና ቫይረስ እንጠብቅ!