​የጣና ሞገዶቹ የመስመር ተከላካይ የጨዋታ ቅጣት ተላለፈበት

[iframe src=”https://bbc.com/” width=”1%” height=”1″]

ባህር ዳር ከተማ እና ድሬዳዋ ከተማ ያለ ግብ አቻ ሲለያዩ በጉዳት ምክንያት በጨዋታው ያልተሳተፈው ተከላካይ በአወዳዳሩው አካል የ3 ጨዋታዎች ቅጣት ተላልፎበታል።

የቤትኪንግ የኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ የ13ኛ ሳምንት ጨዋታዎች ከትናንት በስትያ ፍፃሜያቸውን ማግኘታቸው ይታወቃል። በአብዛኛው የጨዋታ ሳምንቱ በተገባደደ ማግስት የሊጉ የውድድር አመራር እና ሥራ-አስፈፃሚ ኮሚቴ የዲሲፕሊን ውሳኔዎችን ወስኖ ይፋ የሚያደርግ ሲሆን በአሁኑ ግን ትንሽ ዘግየት ብሎ ዛሬ ውሳኔዎችን አሳልፏል።

አክሲዮን ማኅበሩ ከደቂቃዎች በፊት ይፋ ካደረጋቸው የዲሲፕሊን ውሳኔዎች መካከል ደግሞ የባህር ዳር ከተማው የመስመር ተከላካይ አህመድ ረሺድ የሦስት ጨዋታዎች ቅጣት እንደተላለፈበት ያመላክታል። ተጫዋቹ በጉዳት ምክንያት በጨዋታው ባይሳተፍም ጨዋታው ከተገባደደ በኋላ ወደ ሜዳ በመግባት ዳኞችን አፀያፊ ስድብ ስለመሳደቡ እና በፀጥታ አካላት ከሜዳ እንዲወጣ ስለመደረጉ ሪፖርት ቀርቧል በሚል የሦስት ጨዋታዎች እና የ3 ሺ ብር ቅጣት እንደተላለፈበት ተመላክቷል።

ከባህር ዳር ጋር በተያያዘ የቡድን መሪው አቶ ሔኖክ ሀብቱም ተመሳሳይ ጥፋት አጥፍተዋል በሚል ስድስት ጨዋታ እና አምስት ሺ ብር እንዲቀጡ ተወስኗል።