ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በዛሬው እለት ከአሰልጣኝ ጸጋዬ ኪዳነማርያም ጋር በስምምነት መለያየቱ እርግጥ ሆኗል፡፡ አሰልጣኝ ጸጋዬ ኪዳነማርያም በንግድ ባንክ እስከ ሰኔ 30 ቀን 2009 በክለቡ የሚያቆያተው ኮንትራት ቢኖራቸውም ከክለቡ ጋር ባደረጉት ውይይት ለመለያየት ከስምምነት ደርሰዋል፡፡
ክለቡ እና ፀጋዬ ለመለያየት ያበቃቸው ምክንያት ይፋ ባይሆንም አሰልጣኙ ከውድድር ዘመኑ መጀመርያ ጀምሮ የሚፈልጉትን ማሟላት ባለመቻሉ ደስተኛ እንዳልሆኑና ለመለያየታቸውም ምክንያት እንደሆነ ከክለቡ አካባቢ ያገኘነው መረጃ አመልክቷል፡፡
በሊጉ 15ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አሰልጣኝ ጸጋዬን በ5 ጨዋታ ቅጣት ማጣቱን ተከትሎ ያለፉትን 2 ተከታታይ ጨዋታዎች በምክትል አሰልጣኙ ሲሳይ ከበደ እየተመራ ወደ ሜዳ ገብቷል፡፡
አሰልጣኝ ጸጋዬ ከ1990ዎቹ ጋማሽ ጀምሮ በኢትዮጵያ ፕሪምየር ሊግ ክለቦች የሰሩ ሲሆን ከንግድ ባንክ በፊት በትራንስ ኢትዮጵያ ፣ ሀረር ሲቲ (የቀድሞው ሀረር ቢራ) እና ኢትዮጵያ ቡና አሰልጣኝነት አሳልፈዋል፡፡