ኢትዮጵያ ቡና የተለያዩ ተጫዋቾችን ለማስፈረም ጥረቱን ቀጥሏል፡፡ ውል የጨረሱ እና የታገዱ ተጫዋቾችን እያሰናበተ የሚገኘው ክለቡ አዳዲስ ተጫዋቾችን ለማስፈረም እንዲሁም ውል የጨረሱ ተጫዋቾችን ውል የማደስ ስራን ዕየሰራ ነው፡፡
ክለቡ ከሃዋሳ ከነማው የመሃል ተከላካይ ግርማ በቀለ ጋር ስሙ ተያያዟል፡፡ ግርማ ከኢትዮጵያ ቡና የአሰልጣኞች ስታፍ ጋር የተገናኘ ሲሆን ቡናን ለመቀላቀል ድርድር ላይ መሆኑን ለማወቅ ችለናል፡፡ ግርማ በሃዋሳ ከነማ ውሉን ለማደስ የሚችልበት ዕድልም እንዳለ ታውቋል፡፡ ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን መመረጥ የቻለው ግርማ የሃዋሳ ከነማ ተከላካይ መስመርን በመምራት ይታወቃል፡፡ የሃዋሳ ከነማም ምክትል አምበል ነው፡፡
ስሙ በከፍተኛ ደረጃ ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር የተያያዘው አስቻለው ግርማ ከቡና ጋር ድርድር ላይ ነው፡፡ ወደ ቅዱስ ጊዮርጊስ ለመሄድ ሰፊ ዕድል ያለው አስቻለው ለዕረፍት ባሌ ይገኛል:: አጥቂው ቢኒያም አሰፋም ከቡና ጋር ለመቀጠል ድርድር ላይ ነው፡፡ ነገር ግን ቢኒያም ወደ ኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ሊዛወር ይችላል፡፡
ታግዶ የነበረው ተከላካዩ ሚሊዮን በየነ መከላከያን ተቀሏቅሏል፡፡