ዳሽን ቢራ የአዲስ አበባ ከተማ ዋንጫ ላይ ይሳተፋል

በየአመቱ በአዲስ አበባ እግርኳስ ፌዴሬሽን አዘጋጅነት የሚካሄደው የአዲስ አበበ ከተማ ዋንጫ የዘንድሮ ተጋባዥ ክለቦች ጉዳይ እልባት አግኝቷል፡፡ ከአዳማ ከነማ ጋር የሚሳተፈው ሌላኛው የክልል ክለብም ዳሽን ቢራ ሆኗል፡፡

ፌዴሬሽኑ ከዚህ ቀደም እንዲሳተፍ ጥያቄ ያቀረበው ለወላይታ ድቻ ቢሆንም ድቻ ምላሽ ሊሰጥ ባለመቻሉ ግብዣው ወደ ዳሽን ዞሯል፡፡ የጎንደሩ ክለብ በአምናው ውድድር ላይ በተጋባዥነት መካፈሉ የሚታወስ ነው፡፡

የዘንድሮው የአዲስ አበባ ከተማ ዋንጫ ከኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን ካሌንደር ጋር ተጋጭቷል፡፡ ውድድሩ ይጀመራል የተባለው በመጪው ቅዳሜ ቢሆንም በውድድሩ ላይ ይሳተፋሉ የተባሉት ቅዱስ ጊዮርጊስ እና መከላከያ የአሸናፊዎች አሸናፊ ውድድር ጨዋታቸውን እሁድ ያደርጋሉ፡፡ ነገ ጋዜጣዊ መግለጫ ይሰጣል ተብሎ የሚጠበቀው ፌዴሬሽኑ የውድድሩ መደራረብ ጉዳይ ላይ ያለው ነገር ባይኖርም ነገ 5፡00 ላይ በወወክማ በሚሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ውድድሩን አስመልክቶ ያሉትን ውዥንብሮች ያጠራል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ የእጣ ማውጣት ስነስርአቱም አብሮ ይከናወናል፡፡

ፌዴሬሽኑ ወድድሩ ከመስከረም 22 እስከ ጥቅምት 7 እንደሚካሄድ ማስታወቁ የሚታወስ ነው፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published. Required fields are marked *