በቡርኪና ፋሶ በተከሰተው የፖለቲካ አለመረጋጋት ምክንያት ላልተወሰነ ጊዜ ተራዝሞ የነበረው የአለም ከ20 አመት በታች ሴቶች ማጣርያ የመጀመርያ ጨዋታ በመጪው ቅዳሜ መስከረም 22 ቀን 2008 ይካሄዳል፡፡ የካፍን ውሳኔ ተከትሎ ተበትኖ የነበረው የኢትዮጵያ ከ20 አመት በታች ሴቶች ብሄራዊ ቡድንም ዛሬ ልምምድ ማድረግ ጀምሯል፡፡ በአሰልጣኝ አስራት አባተ የሚመራው ቡድኑ ዛሬ በ10 ሰአት ለል ያለ ልምምድ ያደረገ ሲሆን 17 ተጫዋቾችም ተሳትፈዋል፡፡
ከ20 አመት በታች ቡድኑ አሰልጣኝ አስራት አባተ ስለ ዝግጅታቸው ስለ ተጋጣሚያቸው እና አጠቃላይ ስለ ቡድኑ ጉዳይ ለሶከር ኢትዮጵያ የሰጡትን አስተያየት እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡
ስለ ዝግጅታቸው
ከቡርኪና ፋሶ ጋር ልናደርገው የነበረው ጨዋታ መሰረዙን ስናውቅ በዓልም ስለነበር እረፍት ሰጥተናቸው ነበር፡፡ የ4 ቀን እረፍት አድርገው ስለነበር በዛሬው ልምምድ ላይ የመዳከም ስሜት ይታይባቸው ነበር፡፡ ለዛም ብለን ቀለል ያለ ልምምድ እንዲያደርጉ አድርገናል፡፡ ነገ ግን 3፡00 እና 10፡00 ላይ ጠንካራ ልምምድ እናደርጋለን፡፡
ስለ ተጋጣሚያቸው
የቡርኪና ፋሶ ብሄራዊ ቡን ጠንካራ ተጋጣሚ ነው፡፡ በመጀመርያው ማጣርያ አልጄርያን ጥለው ነው የመጡት፡፡ጠንከራ እንሆኑ ስለምናውቅ እኛም ጠንክረን እንገባለን፡፡
ቡርኪናዎች እኛን አሸንፈው ወደ አለም ዋንጫው በመጓዝ በሃገራቸው ያለውን አለመረጋጋት ለማብረድ እንደሚፈልጉ እናውቃለን፡፡ እኛም ሃገራቸው ሰላም እንድትሆን እንፈልጋለን፡፡ ነገር ግን አሸንፈን ለመምጣትና የወከልነውን ህዝብ ለማስደሰት ተዘጋጅተናል፡፡
የስብስቡ ሁኔታ
ተጫዋቾቹ የአእምሮ ጥንካሬያቸው እንደ እድሜያቸው አይደለም፡፡ ፈጣን እና ነገሮችን በፍጥነት የሚረዱ ስለሆኑ አልቸገርም፡፡ ከልምምድ በኋላ ያናገርናቸው በቡርኪና ፋሶ ስለተፈጠረው ነገር ነበር፡፡ ነገር ግን የመረበሽ ስሜት አይታይባቸውም፡፡ ከካሜሩን ጋር ያደረግናቸው ሁለቱ ጨዋታዎች ለተጫዋቾቼ በስነልቡናው በኩል በጣም ጠቅሟቸዋል፡፡
የኮንትራት ሁኔታ
አሁን ላይ ምንም ቅሬታ ማቅረብ አልፈልግም፡፡ ቡድኑን ከያዝኩበት ጊዜ ጀምሮ ፌዴሬሽኑ በሚያስፈልገው ነገር ሁሉ ተባብሮኛል፡፡ የሚያስፈልጉ ነገሮችን በምጠይቅበት ጊዜ ሁሉ ተሟልቶልኛል፡፡ ግንኙነቴም መልካም ነው፡፡ በኮንትራት ጉዳይ ግን ቡድኑን ለረጅም ጊዜ መያዝ እፈልግ ነበር፡፡ የ3 ወር ኮንትራት እና በደሞዜ ላይ የ10ሺ ብር ጭማሪ አድርገውልኛል፡፡ ፍላጎቴ ግን ከተጫዋቾቹ ጋር ለረጅም ጊዜ መስራት ነበር፡፡ ቅር ቢለኝም ከግል ይልቅ ሃገርን አስቀድሜ ስራዬን በአግባቡ እሰራለሁ፡፡