አሰልጣኝ ዘላለም ሽፈራው ረዳታቸውን አሳወቁ

የወላይታ ድቻ አሰልጣኝ ዘላለም ሽፈራው ረዳት አሰልጣኛቸውን መርጠዋል።

ዋናውና ምክትል አሰልጣኙን ያሰናበተው ወላይታ ድቻ አሰልጣኝ ዘላለም ሽፈራውን ከቀጠረ አንድ ወር ማስቆጠሩ ይታወቃል። ቡድኑን ከተረከቡበት ጊዜ አንስቶ በማጠናከር የተጠመዱት አሰልጣኙ ዛሬ አሰልጣኝ ዳዊት ሀብታሙን ረዳታቸው አድርገው መምረጣቸው ታውቋል።

ወጣቱ አሰልጣኝ ዳዊት ሀብታሙ በአዳማ ተስፋ ቡድን በጀመረው የአሰልጣኝነት ህይወቱ በርካታ ወጣቶችን በማፍራት የሚታወቅ ሲሆን በመቀጠል በለገጣፎ ለገዳዲ ከረዳት አሰልጣኝነት እስከ ዋና አሰልጣኝነት ያለፉትን አምስት ዓመታት አገልግሏል። ከ2011 ጀምሮ በዋና አሰልጣኝነት ቡድኑን ሲመራ የቆየው ዳዊት በዛው ዓመት ቡድኑን ለፕሪምየር ሊግ ለማብቃት እስከመጨረሻው ጨዋታ ሲፎካከር የነበረ ሲሆን ዓምናም ሊጉ እስከተቋረጠበት ጊዜ ድረስ ምድቡን ሲመራ ቆይቷል።

በቅርቡ ከለገጣፎ ጋር የተለያየው አሰልጣኙ ነገ ወደ ባህር ዳር በማቅናት ከቡድኑ ጋር በመቀላቀል የአሰልጣኝ ዘላለም ረዳትነት ሥራን እንደሚጀምር ይጠበቃል።


© ሶከር ኢትዮጵያ