“በሜዳ ላይ የሚሰጡ ካርዶችን እንዲነሳላቸው የሚያደርገው አበበ ገላጋይ ነው” ዳዊት አሳምነው

በኢትዮጵያ እግርኳስ ፌዴሬሽን እና በዳኞችና ታዛቢዎች ማኅበር መካከል እየተካሄደ በሚገኘው ስብሰባ ላይ ንግግር ያደረገው ኢንተርናሽናል ዋና ዳኛ ዳዊት አሳምነው የስራ አስፈፃሚ አባል እና ሊግ ኮሚቴ ሰብሳቢ የሆኑት አቶ አበበ ገላጋይ ለዳኞች ስራ እንቅፋት መሆናቸውን ገልጿል።

” ዳኞች ውሳኔ ለመወሰን የተቀመጠላቸው መስፈርቶች አሉ።  ለምሳሌ ተጫዋች በጨዋታ ላይ ሲያጠፋ የሚሰጠው የማስጠንቀቂያ ቢጫ ካርድ ወይም ቀይ ካርድ ዳኛው ሲሰጥ የተቀመጡ ሰባት መስፈርቶች አሉ። በእነዚህ መስፈርቶች መሰረት ቀይ ካርድ ወይም ቢጫ ካርድ እንሰጣለን። ሆኖም ይህ እየተሻረ ነው። አንድ ተጫዋች አራት ጨዋታ በቀይ ካርድ ምክንያት ተቀጥቶ በማግስቱ በምን መልኩ ቀይ ካርዱ እንደሚነሳ አናቅም። አንዳንድ ተጨዋቾች እንድያውም ቀይ ካርድ ስንሰጣቸው ” ችግር የለውም አንተ ቀይ ካርድ ብትሰጠኝ ነገ የሚያነሳልኝ አካል አለ” እያሉ ያፌዙብናል። ይሄን የሚያነሳው ሰው እዚህ የለም ቢኖር ጥሩ ነበር። ይህን የሚያደርገው የፌዴሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ አቶ አበበ ገላጋይ ነው። ክለቦች እንዳይጎዱ እያለ ፤ ስለዚህ ይህ መቅረት አለበት ፊፋ ያስቀመጠው ህግ መከበር አለበት ። ” ብሏል።
” ይህ የዳኛ ውሳኔ በግለሰቦች የሚሻርበት መንገድ “የኪራይ ሰብሳቢነት” መንፈስ ይንፀባርቅበታል ” ሲል የተናገረው ደግሞ ፌዴራል ረዳት ዳኛ ማርቆስ ቱፋ ነው።
– የአበበ ገላጋይን ምላሽ ከቆይታ በኋላ ይዘን እንቀርባለን።