​የአሰልጣኞች አስተያየት | ድሬዳዋ ከተማ 0-0 ባህር ዳር ከተማ

[iframe src=”https://bbc.com/” width=”1%” height=”1″]

ያለ ጎል ከተጠናቀቀው የምሽት ጨዋታ ፍፃሜ በኋላ አሰልጣኞች አስተያየታቸውን በተከታዩ መልክ ሰጥተዋል፡፡

አሰልጣኝ ፉአድ የሱፍ – ድሬዳዋ ከተማ

ስላለማሸነፋቸው ምክንያት

“ምክንያቱ የአጨራረስ ችግር ነው። እንዳየነው ብዙ የጎል አጋጣሚዎችን አግኝተናል ፤ ግን ያው የአጨራረስ ችግሮች ነበሩ፡፡ በዛ የተነሳ ብዙ ጎሎችን ልናባክን ችለናል እንደውም የገባ ኳስ ሁሉ ለእነርሱ አውጥተናል ከዕረፍት በፊት፡፡

በውጤቱ ደስተኛ ስለመሆናቸው

“አዎ ምንም አይከፋም ከመሸነፍ ይሻላል፡፡

ቡድን እየመሩ ስለሚያሳዩት የተለያየ እንቅስቃሴ

“አላውቅም ጉጉትም ሊሆን ይችላል። ዛሬ ወስነን ነበር የመጣነው ፤ ተነጋግረን መጥተናል። ልጆቼ የምፈልገውን ነገር ነው ያሳዩኝ። ያው ዕድልም ከእኛ ጋር አልነበረችም እንጂ ከጨዋታ ጨዋታ እያሻሻልን ዛሬ ደግሞ ህዝቡን የሚያማረካ ነገርን ነው ያሳየነው። ደስ ብሎኛል በውጤቱ ብከፋም ባደረግነው ተጋድሎ በጣም ደስ ብሎኛል፡፡

አብዱራህማን ሙባረክን ጥሩ አለመሆኑን ተከትሎ ስለ ዘገየው ቅያሪ

“ዘግይተናል ግን መጨረሻ ላይ የሆነ ነገር ያደርግልናል ብለን ነበር ፤ የጠበቅነው ሳይሆን ቀርቷል። ግን ሌሎቹ በጣም ጥሩ ነበሩ እሱም የሚከፋ ነገር አልነበረም ሄኖክን በእርሱ ቀይረናል ፤ ጥሩ ነው፡፡”

አሰልጣኝ አብረሃም መብራቱ – ባህር ዳር ከተማ

ቡድኑ ኢላማውን የጠበቀ ሙከራ አለማድረጉ

“ለእኔ ጨዋታው ለሁለታችንም ጥሩ ነበር ማለት እችላለሁ፡፡ ድሬዳዋዎችም ያሳዩት ፐርፎርማንስ ጥሩ ነው። የእኛም ቡድን ያሳየው ፐርፎርማንስ ጥሩ ነው እና ለሁለታችንም ጥሩ ፉክክር ያሳየንበት ክፍት የሆነ ኳስ ነበር ማለት እችላለሁ፡፡ ከዚህ ውጪ በመጀመሪያው አጋማሽ ላይ በመስመር በኩል እየገባን ቦክስ ውስጥ እየደረስን የምናመክናቸው ኳሶች ወደ ግብ ቢቀየሩ ኖሮ የተሻለ ውጤት ማስመዝገብ እንችል ነበር፡፡ከዚህ በተረፈ ግን ፈጣን ጨዋታ ነበር። የነበረው እንቅስቃሴው ጥሩ ነበር እና ተጫዋቾቼ ቢያንስ በዚህ ፈታኝ ጨዋታ ውስጥ በርካታ ተጫዋቾች በጉዳት በሌሉበት ጊዜ ነጥብ ይዘን መውጣታችን በራሱ ትልቅ ነገር ነው ብዬ የማስበው፡፡

በጉዳት ስላልነበሩ ተጫዋቾች ተፅዕኖ

“የገቡ ተጫዋቾች የሚችሉትን ሁሉ አድርገዋል ፤ በደንብ ፐርፎርም አድርገዋል፡፡ ለምሳሌ አቢን እየሁ (ፍቅረሚካኤል) ከሦስት ወራት በኋላ ነው ዛሬ ወደ ሜዳ የገባው። ግን ከአምበልነቱ በተጨማሪ ሜዳው ላይ በተሻለ ተንቀሳቅሷል። ግን ከሜዳ ስለራቀ ማች ፊትነሱ ስላልነበረ ወደ መጨረሻ ላይ እየወረደ መጥቷል፡፡ለዛም ነው መሀል ላይ ትንሽ የበለጡን ከዚህ ውጪ ግን በእርግጥ እነዚህ የተጎዱት ሰባት ያህል ተጫዋቾችን ማጣት በጣም ከባድ ነው። የገቡት ግን የሚችሉትን ሁሉ አድርገው ነጥብ ይዘን መውጣታችን ለሚቀጥለው ጥሩ መነሻ ይሆነናል፡፡

ስለ ግርማ ዲሳሳ ቀይ ካርድ

“እንዲህ ነው ማለት በጣም ከባድ ነው፡፡ ምስሉን በደንብ ስላላየሁት የተሰጠውን ጥፋት ሳይሆን የኔ ጥርጣሬ ይሄ ተጫዋች ግርማን አልፎት ቢሄድ በሌሎች የእኛ ተከላካዮች ሊሸፈን ይችል ነበር፡፡ ምን አልባት የመጨረሻ ሰው ነው ብሎ ከሆነ የሰጠው አሁንም በትክክል ፊልሙን ማየት ያስፈልጋል፡፡ ዞሮ ዞሮ የዳኛውን ውሳኔ በፀጋ መቀበል ነው፡፡ትንሽ ግን ልጁ ቀይ ካርድ አይቶ ካረፈ በኋላ ዛሬ ነው የጀመረው አንደገና ደግሞ በቀጥታ ቀይ ካርድ ለሌሎች ጨዋታዎች እንዲያርፍ መደረጉ በልጁ ፐርፎርማንስ ላይ ተፅእኖ ይፈጥራል፡፡ባለን ጉዳት ላይ በእኛ ተከላካይ ላይ ክፍተት ይፈጥርብናል በተረፈ የዳኞችን ውሳኔ በፀጋ እንቀበላለን፡፡”