ቡማሙሩ ማምሻውን ልምምዱን ሰርቷል

i>በኮፌዴሬሽን ካፕ የቅድመ ማጣርያ ጨዋታውን ከፋሲል ከነማ ጋር የሚያደርገው የብሩንዲው ቡማሙሩ ማምሻውን ልምምዱን አድርጓል።

ነገ በባህር ዳር ዓለም አቀፍ ስታዲየም በአፍሪካ ኮፌዴሬሽን ካፕ ፋሲል ከነማ ከብሩንዲው ቡማሙሩ ጋር በዘጠኝ ሰዓት የሚያደርጉት ጨዋታ ተጠባቂ ነው። ለዚህ ጨዋታ የፋሲል ተጋጣሚ የሆነው ቡማሙሩ ከጨዋታ ቀኑ ቀደም ብሎ ይገባል ሲባል ዘግይቶ ዛሬ አመሻሽ አስር ሰዓት መድረስ ችሏል።

ወደ አስራ አምስት የሚጠጉ ተጫዋቾችን እና የተቀሩ የቡድኑ አባላት በመያዝ ባህር ዳር የደረሰው ቡድኑ ምሽቱ 12:45 ላይ ነገ ጨዋታውን በሚያደርግበት ባህር ዳር ስታዲየም በመገኘት የተወሰነ ምክክር በማድረግ ሁለት ዙር ሙሉ ሜዳውን ከሮጡ በኋላ በጣለው ከባድ ዝናብ ምክንያት ልምምዳቸውን አቋርጠው ወዳረፉበት ዋተር ፍሮንት ሆቴል አቅንተዋል።

ልዑካን ቡድኑ አስቀድሞ ወደ ባህር ዳር ያልመጣው በገንዘብ እጥረት ጉዟቸው በመስተጓጎሉ እንደሆነ ታውቋል። በመጨረሻም የብሩንዲ መንግሥት ድጋፍ አድርጎላቸው ፍላይት ሞልቶባቸው በኢትዮጵያ አየር መንገድ ማምሻውን መግባታቸውን ያገኘነው መረጃ ያመለክታል።

ከደቂቃዎች በኋላ ቡድኑን አስመልከተው ዋናው አሰልጣኙ የሰጡትን አስተያየት ይዘን የምንመለስ ይሆናል።